ኢትዮጵያና ሩሲያ የኒውክሌር ኢነርጂን ለሰላማዊ ዓላማ ለመጠቀም ከዚህ ቀደም የደረሱትን ስምምነት ወደ ተግባር የሚቀይር ዝርዝር የድርጊት መርሃ ግብር በአዲስ አበባ መፈራረማቸው ተገልጿል።
በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የሩሲያ ግዙፍ የኒውክሌር ኮርፖሬሽን (Rosatom) ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኒኮላይ ስፓስኪ እና የኢትዮጵያ ኒውክሌር ኢነርጂ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ሳንዶካን ደበበ የተገኙ ሲሆን፤ በሁለቱ አገራት መካከል ስትራቴጂካዊ ውይይት አካሂደዋል።
ይህ አዲስ ስምምነት ባለፈው መስከረም ወር በሞስኮ የተፈረመውን ስምምነት መሠረት በማድረግ፣ የኒውክሌር ኃይል ፕሮጀክቶችን በቀጥታ ወደ ሥራ ለማስገባት የሚያስችሉ ተግባራትን ያካትታል።
ሰነዱ የአገሪቱን የኃይል አቅርቦት አቅም ለማሳደግ የሚያስፈልጉ የሕግ ማዕቀፎችን ማዘጋጀት፣ የመሠረተ ልማት ግንባታና በዘርፉ የሰለጠነ የሰው ኃይል ማፍራት ላይ በትኩረት እንደሚሠራ ተገልጿል።
ከንጹህ የኃይል አቅርቦት ባለፈ፣ ስምምነቱ የኒውክሌር ቴክኖሎጂን ለዘመናዊ ሕክምና እና ለግብርና ምርታማነት ለማዋል የሚያስችል ሲሆን፣ ይህም የዜጎችን ተጠቃሚነት እንደሚያረጋግጥ ታምኖበታል።
በተጨማሪም ይህ ትብብር በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግርና ዓለም አቀፍ የደህንነት መስፈርቶችን የተከተለ መሆኑ ተመልክቷል።
