ባንኩ የሱፐር አፕ ተጠቃሚዎችን ለማበረታት እንዲሁም የአገልግሎቱን ተደራሽነት ለማስፋት የቲክቶክ ይዘት ፈጠራ ውድድር ማዘጋጀቱን ይፋ አድርጓል።
በዚህ ውድድር ለሚያሸንፉ የይዘት ፈጣሪዎች በድምሩ ስድስት ሚሊዮን ብር የገንዘብ ሽልማት እንዳዘጋጀ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የንግድ ሥራ ትምህርት ቤት (ኮሜርስ) በተዘጋጀ ስነ ስርአት ላይ ተነግሯል።
በዳሸን ሱፐር አፕ ቲክቶክ ቻሌንጅ አሸናፊ ለመሆን ይዘት ፈጣሪዎች ስለ ዳሸን ባንክ ሱፐር አገልግሎቶች የሚገልፅ የቲክቶክ ቪዲዮ በመስራት ማጋራት ይጠበቅባቸዋል ተብሏል።
የሰሩት ቪዲዮ በቲክቶክ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ዕይታ ሲያገኝ፣ በዳሸን ሱፐር አፕ ውስጥ በሚገኘው የዳሸን ክሬቲቭ አዋርድ መተግበሪያ ድምፅ የሚሰጥበት ይሆናል ነው የተባለው፡፡
በመጨረሻም ከፍተኛ ደምፅ በማግኘት አንደኛ ለሚወጣ ይዘት ፈጣሪ 3 ሚሊዮን ብር፣ ሁለተኛ ለሚወጣ 2 ሚሊዮን ብር እንዲሁም ሶስተኛ ለሚወጣ ዳሸን ባንክ 1 ሚሊዮን ብር ሽልማት ይሰጣል ተብሏል፡፡
በዕለቱ ይፋ የተደረገው ሌላው አገልግሎት የዳሸን ስታር ሪፈራል ፕሮግራም ሲሆን፣ ፕሮግራሙ የዳሸን ሱፐር አፕ መተግበሪያ ተጠቃሚዎች በዙሪያቸው የሚገኙ ሰዎች እንዲጠቀሙበት በማድረግ የማበረታች ክፍያ እንዲያገኙ ለማስቻል የቀረበ አገልግሎት መሆኑ ተጠቅሷል፡፡
ባንኩ ከማስተር ካርድ ጋር በመተባበር የተለያዩ ዓለም አቀፍ ክፍያዎችን መክፈል የሚያስችለው የዳሸን ቨርቹዋል ካርድ አገልግሎትም በዛሬው ዕለት ይፋ አድርጓል።
