የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት (ኢባትሎ) ሀገሪቱ ከውጭ የምታስገባውን የነዳጅ ምርት የማጓጓዝ ሥራ ከ40 ዓመታት በኋላ በድጋሚ መጀመሩን አስታወቀ። ተቋሙ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ከናይጄሪያ የተገዛን የኤቪዬሽን (የአውሮፕላን) እና የናፍጣ ነዳጅ በቻርተር መርከቦች ማጓጓዝ ችሏል።
በሆርሙዝ ባህር ሰርጥ አካባቢ በተቀሰቀሰው ግጭት ምክንያት በተፈጠረው የትራንስፖርት መስተጓጎል እና በሀገር ውስጥ እየጨመረ የመጣውን የነዳጅ ፍላጎት ለማሟላት መንግሥት የነዳጅ ግዢ ምንጮቹን እያሰፋ ይገኛል።
በዚህም መሠረት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ያለበትን ከፍተኛ የአውሮፕላን ነዳጅ ፍላጎት ለማሟላትና አማራጭ መስመሮችን ለመጠቀም ከናይጄሪያው ቢሊየነር አሊኮ ዳንጎቴ የነዳጅ ማጣሪያ ፋብሪካ ግዢ ተፈጽሟል።
ኢባትሎ እንዳስታወቀው ተቋሙ መንግሥት በፈጠረው ምቹ ሁኔታ በመጠቀም 120 ሺህ ሜትሪክ ቶን የአውሮፕላን እና የናፍጣ ነዳጅ በሦስት ተከታታይ ጉዞዎች ወደ ጅቡቲው ሆራይዘን ተርሚናል ማጓጓዝ ችሏል። ይህ ስኬት ነዳጅ የማጓጓዝ ልምድ ላልነበረውና “አቅም የለውም” ተብሎ ለሚታሰበው የሎጂስቲክስ ተቋም ትልቅ የሥራ ክንውን መሆኑን አስምሮበታል ።
