ታዋቂው የፈረንሳይ የሚዲያ ግዙፍ ኩባንያ ካናል ፕላስ፣ የዲኤስቲቪ እና የጎቲቪ የላይኛው ኩባንያ የሆነውን የደቡብ አፍሪካውን መልቲቾይስን በ3 ቢሊዮን ዶላር ለመግዛት ያደረገውን ስምምነት በይፋ አጠናቋል።
ይህ ግዙፍ ግዢ መጠናቀቁን ተከትሎ፣ መልቲቾይስ ሙሉ በሙሉ የካናል ፕላስ እህት ኩባንያ ሆኗል። ኩባንያው ከዚህ ውሳኔ በኋላ በመላው አፍሪካ በዲጂታል የፊልም ማሰራጫዎች፣ በቴክኖሎጂ፣ በአገር በቀል የአፍሪካ ይዘቶችና በስፖርት ስርጭቶች ላይ በከፍተኛ ደረጃ መዋዕለ ንዋይ እንደሚያፈስ አስታውቋል።
ይህ ታሪካዊ ግዢ በአፍሪካ ውስጥ ካሉት ትላልቅ የሚዲያና የመዝናኛ ኩባንያዎች መካከል አንዱን የሚፈጥር ሲሆን፣ ካናል ፕላስ በፍጥነት እያደገ ባለው የአፍሪካ የሚዲያና የዲጂታል ስርጭት ገበያ ውስጥ ያለውን የበላይነትና ተሰሚነት ይበልጥ ያጠናክረዋል ተብሎ ይጠበቃል።
በአህጉሪቱ የሚገኙ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የዲኤስቲቪ ተጠቃሚዎችም በዚህ አዲስ ውህደት ሳቢያ ሰፊና ጥራት ያላቸው ይዘቶችን ለማግኘት አዲስ ዕድል እንደሚከፍትላቸው ተነግሯል።
