ሃይኒከን ኢትዮጵያ ማኅበረ ሕይወት ፎር ሶሻል ዴቭሎፕመንት (ኤም.ኤስ.ዲ) ከተሰኘ መንግሥታዊ ያልሆነ የልማት ድርጅት ጋር በመተባበር፤ በ33 ሚልዮን ብር 75 የሚሆኑ አባዎራዎችን ገቢ የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶችን ማስጀመሪያ የርክክብ ሥነ-ስርዓት አከናውኗል፡፡
ፕሮጀክቱን እንዲተገብርለት ኃላፊነት የሰጠው ማኅበረ ሕይወት ፎር ሶሻል ዴቭሎፕመንት (ኤም.ኤስ.ዲ) ሲሆን፤ በዚህም በከብት ማድለብና ምግብ ማቀነባበር የሥራ ዘርፍ ላይ ያተኮረውን ፕሮጀክት ለተጠቃሚዎቹ አስረክቧል፡፡
ፕሮጀክቱ በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 9 በቂሊንጦ አካባቢ የሚገኙ እና በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ቤተሰቦችን ተጠቃሚ ማድረጉ ተነግሯል፡፡ ፕሮጀክቱ በጠቅላላው በ33 ሚሊዮን ብር ወጪ እየተተገበረ ስለመሆኑም ተገልጿል።
በዚህም ፕሮጀክቱ 75 አባወራዎችን ማለትም 30 በቂሊንጦ እና 45 በኮዬ ፈጬ የሚገኙ ነዋሪዎችን በቀጥታ ተጠቃሚ የሚያደርግ ሲሆን፤ ተጠቃሚዎቹ በእንስሳት ማድለብ፣ በወተት ከብት ማርባት፣ በከብት ማደለብ፣ በዶሮ እርባታ እና በባልትና ንግድ የሚሰማሩ ናቸው ተብሏል።
ሃይንከን ኢትዮጵያ በዚህ ፕሮጀክት ዋና ግብ ያደረገው የችግረኛ ቤተሰቦችን የቤተሰብ ገቢን ማሳደግ እነደሆነ እና ለተጠቃሚዎቹ ደረጃውን የጠበቀ የሥራ ቦታ (ሼድ) መገንባቱ ተገልጿል።
በተጨማሪ የሚረቡትን ከብቶች፣ መኖ፣ እንቁላል ጣይ ዶሮዎች፣ የእንስሳት ሕክምና ድጋፍ እና በምግብ ማቀናበር ለተሰማሩት ደግሞ ጤፍ፣ ገብስ፣ ስንዴ፣ በርበሬ፣ ሽሮና ምጣዶችና ሌሎች ለሥራው የሚሆኑ ግብአቶችን ሰጥቷል፡፡
የዕድሉ ተጠቃሚዎች በአብዛኛው የቤተሰብ ኃላፊ የሆኑ እናቶች ሲሆኑ፤ ወደ ሥራው ከመግባትቸው በፊት ከሥራው ጋር የተያያዙ ስልጠናዎች እንደተሰጣቸው ተነግሯል።
ይህ ፕሮጀክት የገቢ ማስገኛ አቅሞችን ከማሳደግ ባለፈ የሥራ ዕድል ፈጠራ እና ማህበራዊ ትስስርን ለማጠናከር ታልሞ የተነደፈ በመሆኑ፤ ሃይንከን ለዘላቂ የማህበረሰብ ልማት ያለውን ተከታታይ ድጋፍም እንደሚያደርግ ተጠቁሟል።
(አሐዱ ሬዲዮ)
