ኢራን የታጠቁ ወታደራዊ ኃይሎቿ በከፍተኛ ደረጃ የተዘጋጁ መሆናቸውን አስታውቃለች።
በዚህም ኢራን እስራኤልን ለሁለት ዓመታት በየቀኑ የመምታት ወታደራዊ አቅም እንዳላት የሀገሪቱ አብዮታዊ ጥበቃ ጓድ አማካሪ ተናግረዋል።
ሜጀር ጄኔራል ኢብራሂም ጃባሪ ለመህር የዜና ወኪል፤ የእኛ የታጠቁ ኃይሎች በዝግጅታቸው ከፍተኛ ደረጃ ላይ ናቸው ብለዋል።
በአሁኑ ጊዜ ያሉን መጋዘኖች፣ የምድር ውስጥ የሚሳኤል መሠረቶች እና መገልገያዎች በጣም ግዙፍ ከመሆናቸው የተነሳ አብዛኛውን የመከላከል አቅማችንን እና ውጤታማ ሚሳኤሎችን አላሳየንም ሲሉ ገልጸዋል።
ከእስራኤል እና ከአሜሪካ ጋር ጦርነት ቢቀጥል ለሁለት ዓመታት በየቀኑ ሚሳኤል ብንተኩስ ኃይሎቻችን አያልቁም ሲሉ ተናግረዋል ሲል አናዶሉ ዘግቧል።
ከዚህ ቀደም የኢራን አብዮታዊ ጥበቃ ኮርፕስ ማስተባበሪያ ኃላፊ ብርጋዴር ጀነራል መሀመድ ሬዛ ናቅዲ፤ ቴህራን ሙሉ ለሙሉ ወታደራዊ አቅሙ ቢኖራትም ከእስራኤል ጋር በተደረገው ጦርነት 5 በመቶ ወታደራዊ አቅሟን ብቻ ተጠቅማለች ማለታቸው ይታወሳል።
በክብረአብ በላቸው
