ሲብሪን የተባለው ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ድርጅት፣ በኢትዮጵያ እየተከናወኑ ያሉትን የዲጂታል ክፍያ ማሻሻያዎችን ለመደገፍ አዲስ ስትራቴጂካዊ ተነሳሽነት ይፋ አድርጓል።
ይህ እንቅስቃሴ የኢስት አፍሪካን የቴክኖሎጂ ገበያ ለማጠናከር እና ደህንነቱ የተጠበቀ የገንዘብ ዝውውር ሥርዓት ለመዘርጋት ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ እንደሆነ ተጠቁሟል።
ድርጅቱ በኢትዮጵያ የክፍያ ሥርዓት ላይ ባደረገው ጥናት፣ አገሪቱ በአፍሪካ ካሉ ትላልቅ የዲጂታል የክፍያ ማሻሻያ ዕድገት አጋጣሚዎች አንዷ መሆኗን ገልጿል።
የቁጥጥር ማሻሻያዎች እና የዲጂታል ቴክኖሎጂዎች ፈጣን ዕድገት ለዚህ ስኬት መሠረት እንደሆኑ ተመላክቷል።
ለተሻሻለው የክፍያ ሥርዓት ስኬት ከአገር ውስጥ አጋር ጋር መሥራት አስፈላጊ መሆኑን የገለጸው ሲብሪን፣ ከቀዳሚዎቹ የኢንፎርሜሽን ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ አቅራቢዎች አንዱ ከሆነው “ሞቲ ኢንጂነሪንግ” ጋር አብሮ ለመሥራት ስምምነት ላይ ደርሷል።
የዚህ ትብብር ዋና ዓላማ የኢትዮጵያ የባንክ እና የፋይናንስ ተቋማት የዲጂታል ክፍያ አፈጻጸማቸውን እንዲያሳድጉ እና የዕለት ተዕለት ሥራዎቻቸውን በራስ-ሰር እንዲያስተካክሉ መርዳት ነው ተብሏል።
