በባህር ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰማሩ ባለሙያዎች በዓለም ዙሪያ ተመራጭና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ለማስቻል እየተሰራ እንደሚገኝ የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስቴር ለአሐዱ ሬድዮ አስታውቋል።
በዓለም አቀፍ ደረጃም ሆነ በሀገር ውስጥ በዘርፉ ከፍተኛ የሆነ የሰው ኃይል ፍላጎት መኖሩን የገለጹት፤ የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስቴር ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ናቸው።
ሙያው ‘አድካሚና ከማህበራዊ ሕይወት ለረዥም ጊዜ ያርቃል’ በሚል ያደጉ ሀገራት ወጣቶች በብዛት እንደማይሰማሩበት የገለጹም ሲሆን፤ ይህ ደግሞ በማደግ ላይ በሚገኙ ሀገራት ላሉ ባለሙያዎች ትልቅ ዕድል መሆኑን ተናግረዋል።
ነገር ግን በኢትዮጵያ የሚፈለገውን ያክል የሰው ኃይል ካለመኖሩ በተጨማሪ፤ ዓለም ላይ ያለውን ዕድልም መጠቀም እንዳልተቻለ አንስተዋል።
በመሆኑም ይህንን ችግር ለመቅረፍ በርካታ ሥራዎች እየተሰሩ እንደሚገኝ የገለጹት ሚኒስትሩ፤ ከእነዚህም ውስጥ በዘርፉ ብቁና የተማረ የሰው ኃይልን ማፍራት በዋናነት የሚሰራበት መሆኑን ተናግረዋል።
በቂ የባህር ላይ ትራንስፖርት ባለሙያዎችን ለማፍራት ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ እና ከግል ባለሀብቶች ጋር በመሆን ስልጠና እየተሰጠ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።
በዚህ ስልጠና ለሚመረቁ ተማሪዎችም የሥራ ዕድል ጭምር እንደሚመቻች ገልጸዋል።
ሚኒስትሩ አክለውም፤ ለመጀመሪያ ጊዜ በባህር ትራንስፖርት ላይ የሚሰሩ የኢትዮጵያ ሴት ወጣት ባለሙያዎች እንደሚመረቁ አስታውቀዋል።
በርካታ የሰለጠኑ ባለሙያዎችን ማፍራት ከተቻለ እነዚህ ወጣቶች በዘርፉ በዓለም ላይ ተወዳዳሪ እንደሚሆኑ የገለጹም ሲሆን፤ ሀገሪቱም በውጪ ምንዛሬ ገቢ ተጠቃሚ እንደምትሆን ጠቁመዋል።
(አሐዱ ሬዲዮ)
