በትግራይ ክልል ሽሬ ከተማ የሚገኙ 8 የሕዝብ ማመላለሻ ትራንስፖርት ማህበራት ሠራተኞች ያለ በቂ ምክንያት ከሥራ ታግደው የነበሩ ሁሉም ወደ ሥራ እንዲመለሱ መደረጉን የኢትዮጵያ ሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም የትግራይ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት አስታውቋል፡፡
የጽ/ቤቱ ኃላፊ አቶ ጸሐዬ እንባዬ በ10 ወራት ውስጥ ለክልሉ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ከቀረቡለት ቅሬታዎች መካከል ከሥራ የታገዱ የሕዝብ ማመላለሻ ትራንስፖርት ማህበራት ሠራተኞች ወደ ሥራ የመመለስ ጥያቄ እንደሚገኝበት ለአሐዱ ገልጸዋል።
እነዚህ የማህበራት ሠራተኞች አብዛኞቹ የስምሪት ተቋጣጣሪ መሆናቸውን እና በስምንቱ ማህበራት ውስጥ በእያንዳንዳቸው ከ3 እስከ 8 የሚደርሱ አባላቶች እንደሚገኙበትም ተናግረዋል።
ኃላፊው አክለውም በአጠቃላይ በትግራይ ክልል በተያዘው በጀት ዓመት ውስጥ 146 ቅሬታዎች እና ከ2 ሺሕ 100 በላይ አቤቱታዎችን ተቋሙ መቀበሉን አስታውቋል።
አብዛኛዎቹ ከመልካም አስተዳደር ጋር በተያያዘ የሚቀርቡ አቤቱታዎች ሲሆኑ ተገቢውን ማስረጃ በመያዝ እልባት እንዲያገኙ እየተሰራ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል።
በዚህም መሠረት ከቀረቡት ከ2 ሺሕ 100 በላይ አቤቱታዎች መካከል ከ102 በላይ የሚሆኑት ተቀባይነት ያላገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
በዚህም ያለ በቂ ምክንያት ከሥራ ማገድ እና ለተነሳው ቅሬታ ምላሽ እንዳያገኝ አስፈጻሚ አካላት ላይ የሚስተዋሉ ችግሮች ተቋሙ በሥራው ላይ ተግዳሮት እንደሆነበት ገልጸዋል።
የክልሉ የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም ቅርንጫፍ ጽ/ቤት በቀጣይ በተለያዩ ምክንያቶች ጉዳያቸው ሳይፈጸም በሚቀሩ አቤቱታዎች ላይ ትኩረት አድርጎ እንደሚሰራም ኃላፊው አጽንኦት ሰጥተውበታል።
(አሐዱ ሬድዮ)
