የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቲያትር የመግቢያ ትኬት ዋጋን ከ ስምንት ዓመት በፊት ከነበረበት 80 ብር ወደ 200 ብር ማሳደጉን አስታውቋል። ቲያትሩ ከ1948 ዓ.ም. ጀምሮ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ ሲሆን፣ ኪነጥበብ ከፍ ማለት እና መከበር አለበት በሚል ዋጋዉን ለማሻሻል ጥናት ሲደረግ መቆየቱ ተገልጿል።
ይህ ውሳኔ የኪነጥበብን ደረጃ ከፍ ለማድረግ እና የቲያትር ቤቱን አገልግሎት ለማሻሻል ያለመ መሆኑ ተጠቁሟል።
የቲያትር ቤቱ ኃላፊዎች፣ የቲኬት ዋጋው ከዚህ ቀደም በጣም ዝቅተኛ ስለነበር፣ አሁን የተደረገው ጭማሪ ሳይሆን ‘ማሻሻያ’ ነው ሲሉ አብራርተዋል። የዋጋ ማሻሻያው “ማንንም የማይጎዳ መልኩ” መሆኑን በማስረገጥ፣ የቲኬት ዋጋው ለሁሉም ትያትሮች በ200 ብር መወሰኑን ገልጸዋል።
ኦንላይን ትኬት ሽያጭ እና ሌሎች ለውጦች
ከተመሠረተ 70 ዓመታትን ያስቆጠረው ብሔራዊ ቲያትር፣ አዳዲስ ለውጦችን በማምጣት ተመልካቹን ለማርካት መዘጋጀቱን አስታውቋል።
ከለውጦቹ መካከል ተመልካቾች ከየቤታቸው ሆነው ትኬት መግዛት የሚያስችላቸውን ‘ኦንላይን’ የቲኬት ሽያጭ ሥርዓት ማመቻቸቱ ተገልጿል።
በተጨማሪም፣ የቲያትር ቤቱ ኃላፊዎች በቀጣይ ሁሉም ክልሎች የሚሳተፉበት ሥልጠና በብሔራዊ ቲያትር እንደሚሰጥ አስታውቀዋል። ይህ የዋጋ ማሻሻያ እና ሌሎች ተያያዥ ለውጦች የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቲያትርን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማምጣት እና ዘመናዊ አገልግሎቶችን ለመስጠት እንደሚያግዝ ይጠበቃል።
