ቅዳሜ ዕለት ኢራን በባሕረ ሰላጤው በሚገኙ የአሜሪካ አጋር አገራት ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት አጠናክራ መቀጠሏን ሮይተርስ ዘገበ።
አሜሪካ ለሰባተኛ ጊዜ ትናንት ምሽት በኢራን ወታደራዊ ተቋማት ላይ ድብደባ መፈጸሟን አስታውቃለች።
በሁለቱ አገራት መካከል የተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት ከፈረሰ በኋላ ግጭቱ ተባብሶ ቀጥሏል።
ኩዌት የውሃ ማጣሪያዋ በኢራን ሚሳዔል የተመታባት ሲሆን አውሮፕላን ማረፊያዋም በተደጋጋሚ በደረሰበት የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃት ስጋት ምክንያት አገልግሎቱን አቋርጧል።
የኢራን አብዮታዊ ዘብ በኩዌት አሪፍጃን የጦር ካምፕ የሚገኝ የአሜሪካ ጦር ድጋፍ ሰጭ ማዕከል ላይ ጥቃት ፈጽሞ የራዳር ተቋምን ማውደሙን አስታውቋል።
የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን አብዮታዊ ዘቡ በባሕሬን የአሜሪካ ጦር አውሮፕላኖች የተሰባሰቡበትን ሼክ ኢሳ የጦር ሰፈር እና የደኅንነት መረጃ ማዕከልን ማጥቃቱን ዘግበዋል።
ሮይተርስ የዘገባውን ትክክለኛነት ለማጣራት ያደረገው ጥረት አልተሳካም።
“የአሜሪካን ጦር ጭካኔ የሚገታ ዓለም አቀፍ ተቋም ስለሌለ፣ ‘ያጠቃችሁን፣ እናንተም በተመሳሳይ መልኩ አጥቁት’ የሚለውን የቁርአን ትዕዛዝ ከመከተል ውጪ ሌላ አማራጭ የለንም” ሲሉ የአብዮታዊ ዘቡ በመግለጫው አስታውቋል።
ዘቡ በዚህ መግለጫው በአካባቢው የሚገኙ የአሜሪካ አጋሮች ተጨማሪ ጥቃቶች ሊያጋጥሟቸው እንደሚችሉ አስጠንቅቋል።
አርብ ዕለት ሁለቱም ወገኖች በመርከብ እንቅስቃሴ ላይ ያነጣጠሩ እርምጃዎችን የወሰዱ ሲሆን፤ የአሜሪካ የባሕር ኃይል ወደ ኢራን የሚሄዱ መርከቦችን ያገደ ሲሆን ቴህራን በበኩሏ የዓለምን የአንድ አምስተኛ የነዳጅ አቅርቦት የሚተላለፍበት ወሳኝ የውሃ መስመር ላይ ሕግ የጣሱ ያለቻቸው መርከቦች ላይ ማነጣጠሯን አስታውቃለች።
