ኢትዮጵያ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት 468 ሺሕ 967 ሜትሪክ ቶን ቡና ወደ ዓለም አቀፍ ገበያ በመላክ፤ 2 ቢሊየን 653 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ገቢ ማግኘቷን የቡና እና ሻይ ባለስልጣን አስታውቋል።
ገቢው ከታቀደው አንፃር በመጠን 144 በመቶ እንዲሁም በገቢ 147 በመቶ አፈጻጸም የታየበት ሲሆን፤ በዚህ ዓመት የተገኘው ገቢ በቡና የወጪ ንግድ ታሪክ አዲስ ክብረ ወሰን ሆኖ መመዝገቡ ተነግሯል፡፡
በተመሳሳይ በበጀት ዓመቱ 11 ወራት 294 ሺሕ 222 ቶን የሻይ እና ቅመማ ቅመም ምርት ለውጭ ሀገር ገበያ በማቅረብ 1 ቢሊየን 557 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር ገቢ መገኘቱን ባለስልጣን አስታውቋል።
የባለሥልጣኑ የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ሥራ አስፈፃሚ ሳህለ ማሪያም ገብረ መድህን፤ ገቢው ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር 86 በመቶ ጭማሪ እንዳለው ለአሐዱ ገልጸዋል፡፡
ባለስልጣኑ ምርትና ምርታማነትን እና ጥራቱን በጠበቀ መልኩ ዓለም ገበያ ለማቅረብ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
በአገር ውስጥ የተመረተውን ምርት ወደ 10 ዋና ዋና መዳረሻ አገራት በመላክ ይህ ገቢ መገኘት መቻሉን የገለጹ ሲሆን፤ የሻይ ቅጠል ምርት ከሚላክባቸው ሀገራት መካከል እንግሊዝ በቀዳሚነት እንደምትቀመጥ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ የሻይ ቅጠል ምርት ለማምረት ምቹ የሆነች አገር መሆኖን ገልጸው፤ በተለይም ሲዳማ አካባቢ ምቹ አየር ንብረት እና አፈር መኖሩን ተናግረዋል።
