ታዋቂው ኢትዮጵያዊ የቴክኖሎጂ ባለሙያና ሥራ ፈጣሪ ኢንጂነር ቢጃይ ናይከር፣ አፍሪካ የራሷን ሳተላይቶች የምታመርትበትን ግዙፍ የቴክኖሎጂ ማዕከል በቡርኪና ፋሶ ለማቋቋም ከስምምነት መድረሳቸውን በይፋ አስታወቁ።
ኢንጂነሩ ለስፑትኒክ አፍሪካ እንደገለጹት፣ ይህንን ታሪካዊ ፕሮጀክት ዕውን ለማድረግ ከቡርኪና ፋሶ መንግሥት ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመው ወደ ግንባታ ምዕራፍ ተሸጋግረዋል።
ይህ የሳተላይት ማምረቻ መርሃ-ግብር በቡርኪና ፋሶ በሚገኝ የኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ የሚተገበር ሲሆን፣ የአህጉሪቱ ትልቁ የቴክኖሎጂ ማዕከል ሆኖ እንደሚያገለግል ይጠበቃል።
ኢንጂነር ቢጃይ ናይከር “እንደ አንድ ፓን-አፍሪካኒስት፣ የፕሬዝዳንት ኢብራሂም ትራኦሬንና የቡርኪና ፋሶን ታላቅ ራዕይ በመደገፍ አህጉራዊ አሻራችንን ለማሳረፍ እየሠራን ነው” በማለት የፕሮጀክቱን ፋይዳ አስገንዝበዋል።
ይህ ፈር ቀዳጅ ተነሳሽነት አፍሪካ በጠፈር ሳይንስና በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያላትን ጥገኝነት በመቀነስ፣ የራሷን የመረጃና የኮሙኒኬሽን መሠረተ ልማት እንድትገነባ ትልቅ በር ይከፍታል።
በቅርቡ ሥራ ይጀምራል የተባለው ይህ ማዕከል፣ ኢትዮጵያውያን በዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ መድረክ ያላቸውን የላቀ ብቃትና ለአህጉራዊ አንድነት ያላቸውን ቁርጠኝነት ዳግም ያስመሰከረ ሆኗል።
