የፌዴራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት የመስሪያ ቤቶችን የተሽከርካሪ አያያዝና ስምሪትን በተመለከተ ባካሄደው ምርመራ በተለያዩ መ/ቤቶች ዘጠኝ መኪኖች ከናካቴው ጠፍተዋል ብሏል፡፡
ተጨማሪ ስድስት ሞተር ብስክሌቶችም የጠፋባቸው መ/ቤቶችን አግኝቻለሁ ብሏል፡፡
የተቋማቱን ስም ግን በኦዲት ሪፖርቱ አልተጠቀሰም፡፡
በሌላ በኩል የባለቤትነት መታወቂያ ደብተራቸው በሌሎች መ/ቤቶችና ድርጅቶች ስም ተመዝግቦ የተገኘ 595 የመንግስት ተሽከርካሪዎች በኦዲት ምርመራው ተገኝተዋል፡፡
እንዲሁም የሰሌዳ ቁጥር የሌላቸው 13 መኪኖች፣ 10 የሞተር ብስክሌቶችና 20 ትራክተሮች የንብረት አያያዛቸው በተፈተሹባቸው የመንግስት ተቋማት መገኘታቸውን የፌዴራል ዋና ኦዲተር መ/ቤት በሪፖርቱ ተናግሯል፡፡
ሌሎች 146 መኪኖች ፣ 27 ሞተር ብስክሌቶች፣ 18 የቁፋሮ መኪኖች ፣ 1 ሎደርና 1 ትራንክተር የሊብሬ ወይም የባለቤትነት መታወቂያ ደብተር ሊቀርብላቸው አልቻለም ተብሏል፡፡
