ከሰሞኑ የተከሰተው የተለመደው የጉንፋን ዓይነት እንጂ አዲስ ወረርሽኝ አለመሆኑ በጥናት መረጋገጡን የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አስታወቀ።
ከሰሞኑ የተከሰተው ጉንፋን በሰዎች ዘንድ ያለው የህመም ስሜት እና የወረርሽኙ በአጭር ጊዜ መዛመት አዲስ ወረርሽኝ መጥቶ ሊሆን ይችላል በሚል በተለያዩ ሰዎች ላይ ስጋት መፍጠሩን የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር መሳይ ኃይሉ ገልጸዋል።
ይሁን እንጂ በማዕከላዊ ኢንፍሉዌንዛ የምርምር ማዕከል በተደረገው ጥናት መሠረት ምንም ዓይነት አዲስ ወረርሽኝ ወይም በሽታ አለመገኘቱን ዋና ዳይሬክተሩ ለመናኸሪያ ሬዲዮ ተናግረዋል።
ያም ሆኖ የክረምት ወራት መጠናቀቁን ተከትሎ፣ ከመስከረም አጋማሽ ጀምሮ እስከ ታህሳስ ወር መጨረሻ ድረስ በኢትዮጵያ የጉንፋን ወረርሽኝ ሊኖር ስለሚችል ሕብረተሰቡ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አሳስቧል።
በመሆኑም የመስከረም ወር መጨረሻ ላይ እንደመሆናችን መጠን፣ በቀጣይ ወራት የጉንፋን ወረርሽኙ የመተላለፍ መጠን እንዳይጨምር እና በህመሙ እንዳይጠቃ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግና እና ከበሽታው ራሱን እንዲከላከል ለሕብረተሰቡ መልእክት ተላልፏል።
