በቅርቡ ወደ አዲስ አበባ አቅንተው የነበሩት የትግራይ ጊዚያዊ አሰተዳደር ፕሬዜዳንት ታደሰ ወረደ (ሌ/ጀ) ከፌደራል መንግስት በ7 ጉዳዮች አመርቂ ውይይትና መግባባት መድረሳቸው ተገለፀ።
ወደ ግጭት የሚያመሩ ፓለቲካዊ ሁኔታዎች ወደ ሰላማዊ የጠረጴዛ ውይይት ማምጣት ስምምነት ከተደረሰባቸው ጉዳዮች አንዱ ነው።
የጊዚያዊ አስተዳደሩ የፕሬዜዳንት ፅህፈት ቤት ታህሳስ 15/2018 ዓ.ም ውይይት ተደርጎባቸዋል ስምምነት ተደርሶባቸዋል ብሎ መግለጫ ያወጣባቸው ነጥቦች ምንና ምን ናቸው ?
1. የደመወዝና የበጀት ጉዳይ
በክልሉና በፌደራል መንግስት መካከል ከአቅም በላይ በሆነ የሰራተኛ ቅጥር ምክንያት ሳይለቀቀ የቆየው የመንግስት ሰራተኞች የደመወዝ ጭማሪ በጀት እንዲለቀቅ በመደበኛ ዓመታዊ በጀት ላይ የነበረው መሳሳብ እንዲፈታና ወደ ስራ እንዲገባ መግባባት ተደርሷል።
2. የሰገን ወንዝ የውሃ ፕሮጀክት ግንባታ የሚመለከት
ለመቐለ ከተማና አከባቢዋ በቂ የንፁህ የመጠጥ ውሃ በማቅረብ የነዋሪዎች ችግር ይፈታል ተብሎ የሚጠበቀው ፕሮጀክት በመሆኑ አስፈላጊ የግንባታ እቃዎች ተማልተውለት እንዲቀጥል ተወስኗል።
3. ያልተቋራረጠ የነዳጅ አቅርቦት
ለክልሉ ወርሃዊ የነዳጅ ፍጆታ የሚበቃ ነዳጅ ሳይቆራረጥ እንዲገባ ውይይት ተደርጎበታል መፍትሄ ተቀምጦለታል።
4. ተፈናቃዮች ስለ መመለስና ግዛታዊ አንድነት የማረጋገጥ ጉዳይ
ተፈናቃዮች የመመለስና ግዛታዊ አንድነት የማረጋገጥ ጉዳይ ቀጣይነት ባለው ውይይትና የፊት ለፊት ግንኙነት መፍትሄ እየተበጀለት እንዲሄድ መግባባት ተደርሶበታል።
5. በሰላማዊ ውይይት የፓለቲካ ችግሮች የመፍታት ጉዳይ
የግጭት መንገዶች ተዘግተው ለጠረጴዛ ውይይት ቅድሚያ እንዲሰጠው መግባባት ተደርሶበታል ” ራሳችን የፈጠርነው ችግር ራሳችን መፍታት ይገባል ” ተብሏል።
6. የአገራዊ የምክክር ሂደትና አፈፃፀሙ የሚመለከት
ከአገራዊ የምክክር ኮሚሽን ከፍተኛ አመራሮች ውይይት ተካሂደዋል። የትግራዩ የምክክር ሂደት በሌሎች ክልሎች ከሚካሄደው ውይይት በተለየ በጦርነቱ የደረሰ ጉዳት ታሳቢ ባደረገ መልኩ እንዲቀጥል ውይይት ተደርጎበታል መግባባት ተደርሶበታል።
7. አገራዊና ክልላዊ ምርጫ በሚመለከት
በቀጣዩ ወርሃ ግንቦት 2018 ዓ.ም የሚካሄደው ሰባተኛው አገራዊና ክልላዊ ምርጫ በትግራይ ለማካሄድ አስቻይ ሁኔታዎች መኖራቸውና አለመኖራቸው አስመልክቶ ጊዚያዊ አስተዳደሩ በያዝነው ሳምንት ይፋዊ መግለጫ እንዲሰጥ መግባባት ላይ ተደርሷል።
@tikvahethiopia
