በኢትዮጵያና በምስራቅ አፍሪካ ቀጣና የሴቶችን እኩልነት ለማረጋገጥ የወጡ የሕግ ማዕቀፎችና ፖሊሲዎች በተግባር ከመሬት ካለው ተጨባጭ ሁኔታ ጋር ባለመጣጣማቸው፣ ሴቶች አሁንም ለኢኮኖሚ መገለልና ለፍትህ እጦት እየተዳረጉ ይገኛሉ ተብሏል።
ከሰሞኑ በአዲስ አበባ በተካሄዱት የኮሜሳ ስብሰባና የፍትህ ተደራሽነት ምክክር መድረኮች ላይ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የሴቶችና ህጻናት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ሂክማ ኬይረዲን እንደገለጹት፤ ሕጎች በወረቀት ላይ ቢሰፍሩም የአተገባበር ክፍተቱ ግን የሴቶችን የለውጥ ጉዞና ተጠቃሚነት በከፍተኛ ሁኔታ ገድቦታል።
በፍትህ ሥርዓቱ ውስጥ የሕግ ማዕቀፎች ተፈጻሚነትን በተመለከተ ሰፊ ክፍተቶች መኖራቸው የተጠቆሙ ሲሆን፤በዓለም አቀፍ ደረጃ ሴቶች መብቶቻቸውን በተሟላ ሁኔታ የመጠቀም ዕድላቸው 64 በመቶ ብቻ መሆኑና ቀሪው 36 በመቶው በፍትህ ሥርዓቱ ውስጥ ተገቢውን ትኩረት አለማግኘቱ ተመላክቷል።
አብዛኛው የኢትዮጵያ ሴት በሚኖርበት የገጠር አካባቢ ደግሞ የፍትህ ተቋማት መራቅና የሕግ ግንዛቤ ማነስ ሕጎች በወረቀት ላይ ብቻ ተወስነው እንዲቀሩ አድርጓቸዋል።
ከዚህም በተጨማሪ በገጠር አካባቢዎች የሚዘወተሩና ሴቶችን የሚበድሉ ባህላዊ የግጭት አፈታት ሥርዓቶች ከሀገሪቱ ሕግ በላይ ሆነው መገኘታቸው የሕግ ማዕቀፎቹን ውጤታማነት ክፉኛ ቀንሶታል ብለዋል።
በኢኮኖሚው ዘርፍም የሕግ እኩልነትና የፋይናንስ ተቋማት አሰራር አለመጣጣም ሌላኛው ፈታኝ ጉዳይ ሆኗል።
የኢትዮጵያ ሕግ ለሴቶች እኩል የሀብትና የፋይናንስ ተጠቃሚነት መብት ቢሰጥም፤የፋይናንስ ተቋማት አተገባበር ግን አሁንም ትልቅ ክፍተት ይታይበታል።
የፖሊሲዎች አለመናበብ በተለይ በድንበር ተሻጋሪ ንግድ ላይ በተሰማሩ ሴቶች ላይ ለሚደርሱ እንደ ትንኮሳና ማጭበርበር ላሉ ጥቃቶች ተገቢውን የሕግ ከለላ ለመስጠት አዳጋች ማድረጉ ሲነሳ፤በወረቀት ላይ የሰፈሩ ሕጎችንና ፖሊሲዎችን በተግባር ወደ መሬት በማውረድ ረገድ የሚታየውን የአመለካከትና የተቋማዊ ቁርጠኝነት ችግር ለመፍታት የፖሊሲ ማሳለጫዎችና የተጠናከረ ክትትል እንደሚያስፈልግ ተመላክቷል።
