ኢትዮጵያ ከ1986 ዓ/ም ጀምሮ ከ 30 ዓመታት በላይ ስትጠቀምበት የቆየችው ብሔራዊ የኢነርጂ ፖሊሲ ሊሻሻል መሆኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታውቋል።
የፖሊሲው መሻሻል አንዱ ዓላማ የሀገሪቱን የኃይል ምንጭ ስብጥር ማስፋት ነው። በአሁኑ ወቅት 95 በመቶ የሚሆነው የሀገሪቱ የኤሌክትሪክ ፍጆታ የሚሸፈነው ከውኃ ኃይል መሆኑን የገለጹት የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ሞገስ መኮንን በተሻሻለው ፖሊሲ እንደ ነፋስ እና የከርሰ ምድር ሙቀት ወይም ጂኦተርማል ያሉ የኃይል አማራጮችን በማስፋት የውኃ ኃይልን ድርሻ ወደ 70 በመቶ ለማውረድ መታቀዱን ተናግረዋል።
አዲሱ ፖሊሲ በሀገሪቱ ያለውን የኃይል ተደራሽነት የማሳደግ ዓላማ እንዳለውም ተገልጿል። በአሁኑ ወቅት 54 በመቶ ላይ የሚገኘውን ተደራሽነት ፖሊሲው ከጸደቀ በኋላ ባሉት አምስት ዓመታት ውስጥ ወደ 70 በመቶ ለማሳደግ ታቅዷልም ብለዋል።
ሀገሪቱ ከ 30 ዓመታት በላይ የተጠቀመችበት የኃይል ፖሊሲ አሁን ካለው ሀገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ ጋር የማይጣጣም በመሆኑ መሻሻሉ በጎ እርምጃ መሆኑን ተቋሙ ገልጿል።
በረቂቅ ፖሊሲው ዝግጅት ላይ ሙያዊ ድጋፍ በመስጠትና በማማከር የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገራት ባለሙያዎች መሳተፋቸው ተነግሯል።
#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ
