የኤርትራ ማስታወቂያ ሚንስትርና ቃል አቀባይ የማነ ገብረመስቀል፣ ኤርትራ ብሄራዊ የውትድርና አገልግሎትን ተግባራዊ በማድረጓ ሲወነጅሏት የነበሩ የአውሮፓ ኅብረት አባል አገራት፣ የብሄራዊ የውትድርና አገልግሎት ለራሳቸው ብሄራዊ ደኅንነት አስፈላጊ ኾኖ ሲያገኙት ግን የኤርትራን ፈለግ ለመከተል አያቅማሙም በማለት በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሠፈሩት አጭር መልዕክት ተሳልቀዋል።
የማነ በአውሮፓ አገራት ላይ በዚህ መልኩ የተሳለቁት፣ የጀርመን መንግሥት የተጠባባቂ ወታደራዊ ኃይሉን ቁጥር ለመጨመር ሲል ዜጎች በፍቃደኝነት ላይ የተመሠረተ ብሄራዊ የውትድርና አገልግሎት እንዲሠጡ ሰሞኑን ለፓርላማው ረቂቅ ሕግ ማቅረቡን ተከትሎ ነው።
ረቂቅ ሕጉ፣ በፍቃደኝነት ላይ የተመሠረተ ብሄራዊ የውትድርና አገልግሎት የሚሠጡ ዜጎች ቁጥር የተፈለገውን ያህል ካልኾነ፣ መንግሥት የወታደር ምልመላ እንዲጀምር የሚፈቅድ ነው።
የአውሮፓ ኅብረት አባል አገራትን ጨምሮ ምዕራባዊያንና ዓለማቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በኤርትራ ላይ ከሚያቀርቡት ውግዘት ዋነኛው፣ የኤርትራ መንግሥት በዜጎቹ ላይ ገደብ አልባ የብሄራዊ ውትድርና አገልግሎት ጭኖባቸዋል የሚል እንደኾነ ይታወቃል።
(ዋዜማ)
