የኢትዮጵያ የካፒታል ገበያ ባለስልጣን ከሰፊ የፈቃድ ማመልከቻ ግምገማ ሂደት በኋላ ለሦስት አዳዲስ የካፒታል ገበያ አገልግሎት ሰጭዎች ፍቃድ መስጠቱን በይፋ አስታውቋል።
ይህንን ተከትሎም በሀገሪቱ በፈቃድ የሚንቀሳቀሱ የካፒታል ገበያ አገልግሎት ሰጭዎች ጠቅላላ ቁጥር ከ18 ወደ 21 ከፍ ብሏል። ባለስልጣኑ አዳዲሶቹን ተቋማት ከመፍቀድ ባለፈ፣ የሦስቱን አዳዲስ አገልግሎት ሰጭዎች 10 ተሿሚ እንደራሴዎችን እና የ15 የቦርድ አባላትን ሹመት መርምሮ ማፅደቁ ተጠቁሟል።
የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ ፈቃዱን በባለስልጣኑ ዋና መስሪያ ቤት በተዘጋጀ ደማቅ መርሃ ግብር ለሦስቱ አዳዲስ የካፒታል ገበያ አገልግሎት ሰጭዎች አመራሮች በይፋ አስረክበዋል።
በአዲሱ አሰላለፍ መሰረት በሀገሪቱ የሚገኙ የኢንቨስትመንት ባንኮች ቁጥር ወደ 8 ያደገ ሲሆን፣ የሰነደ ሙዓለንዋዮች የኢንቨስትመንት አማካሪዎች ቁጥር ደግሞ ወደ አስራ አንድ ከፍ ማለቱ ተረጋግጧል።
አዳዲሶቹ ፈቃድ የተሰጣቸው የካፒታል ገበያ አገልግሎት ሰጭዎች ፕራይዝዎርዝ ኢንቨስትመንት ባንክ አ.ማ በኢንቨስትመንት ባንክ ዘርፍ፣ ብሉፊን ካፒታል አድቫይዘሪ ኃ.የተ.የግ.ማ በሰነደ ሙዓለንዋይ ኢንቨስትመንት ማማከር ዘርፍ፣ እንዲሁም ሉሚና ካፒታል ኃ.የተ.የግ.ማ በሰነደ ሙዓለንዋይ ኢንቨስትመንት ማማከር ዘርፍ መሆናቸው ታውቋል።
