የኢትዮጵያ መንግስት የህዳሴውን ግድብ እንዲጎበኙና በምርቃት ስነስርአቱም ላይ እንዲገኙ ጥሪ እንዳቀረበላቸው የገለጹት የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ባድር አብደላቲ፤ በታላቁ የህዳሴ ግድብ ላይ እንደማይገኙ ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ አስታውቀዋል፡፡
‹‹ግብዣው ምንም ዓይነት ፖለቲካዊም ሆነ ህጋዊ አመክንዮ የለውም›› ያሉት ሚኒስትሩ፤ ግብፅ ለምርቃቱ እንደማትገኝና ተወካዮችንም እንደማትልክ ገልጸዋል፡፡
ሚኒስትሩ “አል ሾሩክ” ከተሰኘው የግብፅ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ አገራቸው ብሄራዊ የውሀ ደህንነቷን ማስነካት እንደማትፈቅድ አስረግጠው ተናግረዋል፡፡
‹‹የአባይ ውሀ ለድርድር ወይንም ለንግግር የሚቀርብ ሳይሆን ከመላው የግብፅ ህዝብ ጋር የተያያዘ የህልውና ጉዳይ ነው›› ብለዋል፤ ከጋዜጣው ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ፡፡
ባድር አብደላቲ አክለውም፤ ‹‹የግብፅን ስትራቴጂካዊ ጥቅምና የአባይ ውሀ ታሪካዊ ድርሻችንን የሚጎዳ ግድብን እንድንጎበኝ ግብዣ ማቅረብ ተገቢ ነውን?›› ሲሉም ጠይቀዋል፡፡
ባድር አብደላቲ አክለውም፤ ‹‹ስለ ግብዣው ማውራት ትርጉም የለሽና በምንም ስሌት የማይሆን ነው›› ብለዋል፡፡
