የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ ተከትሎ በጾመ ነነዌ ጥቁር ለብሳችኋል በሚል ምክንያት ከሥራና ከደመወዝ መታገዳቸውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፕላንና ልማት ኮሚሽንና የመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ ሠራተኞች አስታወቁ።
የኢትዮጵያየ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ በቤተ ክርስቲያኗ ውስጥ በተከሰተው ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና አስተዳደራዊ መዋቅሮቿን በመጣስ መፈንቅለ ሲኖዶስ በማድረግ በሕገወጥ መንገድ ኤጲስ ቆጶስነት ሢመት በሰጡትና ቤተ ክርስቲያኗ የምታስተዳድራቸውን መንበረ ጵጵስናዎችንና ቢሮዎችን በኃይል በመውረራቸውና ጾመ ነነዌን ምክንያት በማድረግ በመላው ዓለም የሚገኙ ሕዝበ ክርስቲያን ጥቁር ልብስ ብቻ በመልበስ በጾምና በጸሎት ምሕላ በመያዝ በቤተ ክርስቲያን ዓውደ ምሕረት በመገኘት ወደ እግዚአብሔር ጾም፤ ጸሎትና ምሕላ እንድታቀርቡ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን ማቅረቡ አይዘነጋም።
በወቅቱ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዳስታወቀው ጥቁር ልብስ የሚለበሰው በመከራ መጽናት ለመግለጽ እንደሆነ ገልጿል። በመሆኑም “ከጥር 29 እስከ የካቲት 1 ቀን 2015 ዓ.ም ለሦስት ቀናት በጾምና በጸሎት በአንድ ልብ ሆነን ወደ ፈጣሪያችንን እንድንጮህ አደራ እንላለን” ሲል ጥር 26 ቀን 2015 ዓ.ም ሲኖዶሱ መግለጫ አውጥቷል። ይህንን ተከትሎ በመላው ዓለም የሚገኙ ኦርቶዶክሳውያን ውሳኔውን ተቀብለው ሲተገብሩ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፕላንና ልማት ኮሚሽን፣ የመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ ሠራተኞች ወ/ሮ ሙሉ አያሌው፣ ወ/ሮ በለጡ ዘለቀ እና ወ/ሮ የትናየት ተሾመ ጥቁር ለብሰው ወደ ቢሯቸው ሲገቡ የጥበቃ አባላት አትገቡም ይሏቸዋል። በዚህም መሀል ክልከላው በማኅበራዊ ሚዲያ ይሠራጫል። የተቋማችንን ገጽታ አበላሽታችኋል ጥቁር ልብስ ሳልፈቅድላችሁ ለብሳችኋል በሚል በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፕላንና ልማት ኮሚሽን፣ የመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ ሠራተኞች ወ/ሮ ሙሉ አያሌው ወ/ሮ በለጡ ዘለቀ እና ወ/ሮ የትናየት ተሾመን ከሥራና ከደመወዝ እንዳገዳቸው ገልጸዋል። ጉዳዩን የቤተክርስቲያኗ የጠበቆች ቡድን በሕግ አግባብ እንደሚከታተለው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
