” እንደ ሀገር ግብር መሰብሰብ አለበት ልማትም መቀጠል አለበት ፤ የሰው ህይወትም መቀጠል አለበት ፤ ሰው እየተራበ መስራት አይችልም ምርታማ መሆን አይችልም ! “
የኢትዮጵያ የሰራተኛ ማህበራት ኮንፌደሬሽን ዋና ፕሬዘዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ ስለ ገቢ ግብር አዋጁ ምን አሉ ?
” የደመወዝ ገቢ ግብር ከዚህ በፊት መነሻው 600 ብር ነው፤ አሁን በረቂቁ የቀረበው 2,000 ሆኖ ነው።
በመሰረቱ 600 በሆነበት ሰዓት አንደኛ ገንዘብ የመግዛት አቅሙ ትልቅ በመሆኑ ፣ 1 ዶላርም 20 ብር ነበር ያኔ የዛሬ 10 ዓመት አካባቢ ነው ይሄ ነገር የተሻሻለው ፤ ሁለተኛ የመንግሥት ሰራተኞች መነሻ ደመወዝ 600 ነበር ያኔ 600 ለአንድ ሰው ለአንድ ወር ቢያንስ ምግብ መብላት ብቻ ይበቃዋል በሚል ታሳቢ አማካይ ተወስዶ ነው 600 የተባለው።
አሁን ግን 300% ፣ 200% ጨመርን (ማለትም 2000 ብር አደረግን) እሱ አይደለም ዋናው መነሻው ስንት ነው አሁን ? በአጭሩ ፤ እንኳን የኑሮ ውድነቱን ታሳቢ ያደረገ መንግሥት እራሱ ሰራተኛው በ600 ብር ሊያኖረው አይችልም ፤ የኑሮ ውድነቱ ከሚታሰበው በላይ በተለይም በሪፎርሙ መንግሥት በይፋ ያረጋገጠው ታችኛው የሰራተኛ ክፍል ጎድቶታል፤ ‘ ሊቋቋመው አይችልም ‘ በሚል መነሻ ደመወዙን ከፍ አድርጓል ፤ መነሻ ደመወዝን ከፍ ሲያደርግ ይሄን ታሳቢ አድርጓል።
አሁንም ቢሆን እነዚህ ሰዎች መኖር ከማይችል ሰው ግብር አትሰበስብም ፤ በልቶ ከማያድር ሰው ግብር አትሰበስብም። በቀን 2.15 ዶላር የሚያገኝ ሰው ድሃ ነው ከዚያ በታች የሚያገኝ በሙሉ ድሃ ነው ፤ እኛ ደግሞ እዛ ሁሉ አልደረስንም።
እኛ እያቀረብን ያለነው ሃሳብ 8,324 መነሻ ይሁን ነው። እንኳን የኛ ሀሳብ የመንግሥት እራሱ ያስቀመጠው መነሻ ላይ እንኳን አልደረሰም።
ሌላው በፊት የግብር ምጣኔው ከ0 ጀምሮ 10% ፣ 15% ፣ 20% ፣ 25% ፣ 30% ፣ 35% ይቀጥል ነበር አሁን 10%ን ከመሃል አወጡና ከ0 ጀምረው ቀጥታ 15% ነው የገቡት። አሁን ቀጥታ ከ15 ከከፍተኛው ነው ሲጀምር የጀመሩት። ይሄ ትክክል አይደለም።
35% ከየት ጀመረ 14,100 በላይ የሚያገኝ ሰው 35% ግብር ይከፍላል ፤ 35% ከሰራተኛ በአሁኑ የኑሮ ውድነት 15% በእያንዳንዱ በምግብ ዋጋም፣ በሚገዛው እቃም 15% ይጨምራል ይሄ ሲደመር 50% ይመጣል፤ 7% የጡረታ አለ ጡረታ የሚያገኘው ከ60 ዓመት በኃላ አሁን ግን 57% ከደመወዙ ላይ ይሄዳል በቀረችው 43% ፦
– ልጆች ያስተምራል
– ምግብ ይበላል
– ልብስ ይገዛል
– ቤት ይከራያል ምንድነው የሚያደርገው ?
ይሄና ይሄ ብቻ ስላልሆነ ነው ዝም ያልን እንጂ ይሄም ከፍ ብሎ እኮ ይበቃል ማለት አይደለም።
ግን እንደ ሀገር ግብር መሰብሰብ አለበት ልማትም መቀጠል አለበት ፤ የሰው ህይወትም መቀጠል አለበት ፤ ሰው እየተራበ መስራት አይችልም ምርታማ መሆን አይችልም። “
@tikvahethiopia
