ስዊዘርላንድ ለሁለት ዓመት ያክል በኢትዮጵያውያን ዜጎች ላይ ጥላው የነበረውን የቪዛ ገደብ ሙሉ በሙሉ ማንሳቷን የሀገሪቱ ፌደራል ምክር ቤት አስታወቀ።
ሀገሪቱ ውሳኔውን ያስተላለፈችው በ ሸንገን ቪዛ ስምምነት ማዕቀፍ ውስጥ በመሆን ሲሆን ይህም የአውሮፓ ኅብረት ምክር ቤት በቅርቡ የኢትዮጵያ መንግሥት ሕገ-ወጥ ስደተኞችን መልሶ ለመቀበል የተሻለ ትብብር አሳይቷል ማለቱን ተከትሎ የቪዛ ቅነሳ መመሪያዎችን በድጋሚ ሥራ ላይ ለማዋል ካሳለፈው ውሳኔ ጋር የተያያዘ መሆኑን አስታውቋል። ከዚህ ቀደም የቪዛ እገዳ ዋነኛ ምክንያት ኢትዮጵያ ስደተኛ ዜጎቿን ለመቀበል ፈቃደኛ አይደለችም የሚልም ነበር።
ከሁለት ዓመት በፊት የአውሮፓ ኅብረት አንዳንድ የቪዛ ሕግጋትን ለኢትዮጵያውያን ማገዱ የሚታወስ ሲሆን የዚህም ምክንያት በሸንገን ቀጠና ውስጥ ያለ ቪዛ የሚኖሩ የኢትዮጵያ ዜጎችን ወደ ሀገራቸው ከመመለስ አንጻር የነበረው ትብብር አነስተኛ በመሆኑ ነበር።
ስዊዘርላንድ የሸንገን ስምምነት አባል በመሆንዋ ይህንኑ ገደብ ተግባራዊ አድርጋ የቆየች ሲሆን አሁን ላይ በሁለቱ ወገኖች መካከል ያለው ትብብር መሻሻል ማሳየቱን ተከትሎ የአውሮፓ ኅብረት ባለፈው ግንቦት ወር ገደቡን በማንሳቱ ስዊዘርላንድም ውሳኔውን በመደገፍ በዛሬው ዕለት እገዳውን በምክር ቤቷ ሙሉ በሙሉ አንስታለች።
በዚህም መሠረት ከዛሬ ጀምሮ የቪዛ ማቅለያዎች ለኢትዮጵያውያን ዜጎች ተግባራዊ መሆን የሚጀምሩ ሲሆን የማስረጃ ሰነዶች ማቅለል አንዱ ሲሆን የቪዛ ማመልከቻ በሚያስገቡበት ወቅት የሚጠየቁ አንዳንድ ደጋፊ ሰነዶችን የማቅለል ወይም የመተው አማራጭን ያካትታል።
የዲፕሎማቲክ እና የአገልግሎት ፓስፖርት ያላቸው የኢትዮጵያ ዜጎች ከቪዛ ክፍያ የሚያደርጋቸው ሲሆን ከአንድ ጊዜ በላይ ወደ ሀገሪቱ ለመግባት የሚያስችል የቪዛ አገልግሎት እንደገና ጀምሯል።
በተጨማሪም የቪዛ ማመልከቻዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ማለትም በ15 ቀናት ውስጥ ታይተው ምላሽ የሚያገኙ ይሆናል ስትል ስዊዘርላንድ አስታውቃለች።
አዲስ ማለዳ
