ራሳቸውን ‹‹መሪጌታ›› ጽጌ ስጦታው እና ‹‹መሪጌታ›› ምስጢረ መዝገቡ ብለው የሚጠሩ ግለሰቦች በቅድስት ቤተክርስቲያኛችን ሥርዓተ እምነት ላይ በወንጀል የሚያስጠይቅ ድርጊት ፈጽመዋል በሚል ተጠርጥረው የወንጀል አቤቱታ በቀረበባቸው መሠረት የፌደራል ወንጀል ምርመራ ቢሮ በዛሬው ቀን ተጠርጣሪዎችን በሕግ ቁጥጥር ሥር በማዋል የወንጀል ምርመራውን በማጣራት ላይ እንደሚገኝ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን የሕግ ባለሙያዎች ዐቢይ ኮሚቴ አባል ጠበቃ አያሌው ቢታኔ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል።
ጠበቃ አያሌው አያይዘው እንደገለጹት ከግለሰቦቹ በተጨማሪ እንዳልካቸው ዘነበ የተባለ ግለሰብ በተመሳሳይ ከዚህ ቀደም በቤተክርስቲያናችን ላይ ፈጽሞታል ተብሎ በተጠረጠረበት ስም ማጥፋት በቅርቡ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውሎ ቃሉን ሰጥቶ በዋስትና መለቀቁን እና በዐቃቤ ሕግ በኩልም የወንጀል አቤቱታ ክስ ቀርቦ በሒደት ላይ እንደሚገኝ አያይዘው ገልጸዋል።
የሕግ ባለሙያዎች ዐቢይ ኮሚቴ አባል ጠበቃ አያሌው ቢታኔ በሰጡት መረጃ ኮሚቴው ወደ ፊት ጉዳዩን ተከታትሎ የሚያሳውቅ መሆኑን ገልጸዋል።
©EOTC TV
