በክልሉ ያለዉ የነዳጅ ግብይት ህግ እና ስርአትን ተከትሎ እየተከወነ አይደለም ተብሏል።
በዚህም በክልሉ ሰዉ ሰራሽ የነዳጅ እጥረት በመከሰቱ በማህበረሰቡ እንቅስቃሴ ላይ እክል መፍጠሩን ከክልሉ ንግድ ቢሮ ሰምተናል።
የጋምቤላ ክልል ንግድ ቢሮ ሀላፊ ወ/ሮ ኛሞች ጊል በክልሉ ያሉ የነዳጅ ማደያዎች ከተለያዩ የወርቅ አዉጪ ድርጅቶች ጋር እየፈፀሙት ያለዉ ህገ ወጥ ግብይት ዋነኛ ችግር ሆኗል ብለዋል።
ማደያዎች ያመጡትን ናፍጣ እና ቤንዚል ከታሪፍ በላይ ከመሸጣቸዉ በተጨማሪ ነዳጅ በድብቅ በጥቁር ገበያዉ እየወጣ መሆኑ ተገልጿል።
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በክልሉ የማደያ ግንባታዎች መበራከት ተስተዉሏል።
በዚህም ፍቃድ ሰጪ ተቋማት የአስፈላጊነት ግምገማዎችን በማድረግ በህጋዊ ስርአት ብቻ ፍቃድ ሊሰጡ እንደሚገባቸዉ ተጠይቋል።
የክልሉ ንግድ ቢሮ በህገ ወጥ የነዳጅ ችርቻሮ ላይ የተሰማሩ ማደያዎች እና ግለሰቦች ለመቆጣጠር እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑን ገልጿል።
የነዳጅ እጥረት እንዲፈጠር እያደረጉ ነዉ በተባሉ ማደያዎች በመቆጣጠር የነዳጅ ስርጭቱን ማስተካከል እንዲቻል እየተሰራ መሆኑም ተገልጿል።
