የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ለዘመናት ተግባራዊ ሲያደርግ የቆየውንና በሕግ ተወስኖ የነበረውን የ7 በመቶ ዝቅተኛ የቁጠባ ወለድ (Minimum Deposit Saving Rate) በማንሳት፣ ከዚህ በኋላ የወለድ መጠን በገበያ ፍላጎትና አቅርቦት እንዲወሰን መወሰኑን አስታወቀ።
ባንኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ያስላለፈው ይህ ታሪካዊ ውሳኔ፣ ከሐምሌ 2016 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ እየተደረገ ያለውን በወለድ ላይ የተመሰረተ የገንዘብ ፖሊሲ ማዕቀፍ ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ያለመ ነው።
እንደ ብሔራዊ ባንክ የገንዘብ ፓሊሲ ኮሚቴ መረጃ ከሆነ፤ ቀደም ሲል መንግስት ዝቅተኛውን የወለድ መጠን ወስኖ አስቀማጮች በከፍተኛው መጠን ላይ ብቻ እንዲደራደሩ የሚያደርገው አሰራር ተቀይሮ፣ አሁን ግን የወለድ ተመኑ በአስቀማጮች እና በባንኮች መካከል በሚደረግ ነፃ ድርድርና ስምምነት እንዲወሰን በባንኩ ቦርድ ጸድቋል።
የዚህ ፖሊሲ ዋና ዓላማ በኢኮኖሚው ውስጥ የሚዘዋወረውን የገንዘብ መጠን በወለድ በኩል በመቆጣጠር የዋጋ ንረትን ለማረጋጋትና የባንኮችን የውድድር መንፈስ በማሳደግ ቁጠባን ለማበረታታት መሆኑ ተጠቁሟል።
ብሔራዊ ባንክ አክሎም፣ ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲው በዋጋ መረጋጋት ላይ ችግር እንደሚገጥመው በተረዳ ጊዜ ያሉትን የፖሊሲ መሣሪያዎች ሁሉ እንደሚጠቀም አስታውቋል።
የገንዘብ ፖሊሲው አሁን ላይ ከማላላት ይልቅ ይበልጥ ጥብቅ ያደረገዉ ኮሚቴዉ ባንኮች በብሔራዊ ባንክ ዘንድ እንዲያስቀምጡ የሚገደዱት ወርሃዊ አማካይ የመጠባበቂያ ክምችት ምጣኔ ከነበረበት በሁለት በመቶ በማደግ ወደ 10 በመቶ እንዲያድግ ተወስኗል። ዕለታዊ ዝቅተኛው የመጠባበቂያ ክምችት ግን በነበረበት 5 በመቶ እንዲቀጥል ተደርጓል።
