የቱሪዝም ሚኒስቴር ከተለያዩ የቱሪዝም ዘርፍ ባለድርሻ አካላት ጋር በቱሪዝም ፖሊሲ ረቂቅ ሰነድ ላይ ወይይት አካሂዷል፡፡ በመድረኩ መክፍቻ ንግግር ያደረጉት የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ እንደገለጹት ኢትዮጵያ በታሪካዊ፣ተፈጥሯዊ እና ሰው ሰራሽ የቱሪስት ኃብቶች በዓለም ካሉ ሀገራት በቀዳሚ ተርታ የሚያስቀምጥ ሃብት ያላት ናት ብለዋል።
ኢትዮጵያ ከዚህ ቀደም ከአስር አመት በላይ ያስቆጠረ የቱሪዝም ፖሊሲ ስትጠቀም መቆየቷን ሚኒስትሯ አንስተው ለቱሪዝም ዘርፋ የተሰጠውን ትኩረት የሚመጥን የፖሊሲ ማእቀፍ ማዘጋጀት ያስፈልጋል ማለታቸውን ብስራት ሬዲዮ ሰምቷል። አሁን ላይ ለቱሪዝም ዘርፋ የተሰጠውን ትኩረት እንዲሁም አለምአቀፍ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ያለውን መልክ በሚመጥን መልኩ መቃኘት በማስፈለጉ የቱሪዝም ፖሊሲ ክለሳ እንዲደረግ ተወስኗል።
በርካታ ሂደቶችን አልፎ የፖሊሲ ረቂቅ ሰነዱ ከዚህ መድረሱን ያነሱት ሚንስትሯ በርካታ አካላትን ያሳተፈ ውይይት በማድረግ ግብዓት ሲሰባሰብ መቆየቱን አስታውሰዋል። ፖሊስው ተወዳዳሪና ዘላቂ የቱሪዝም ልማትን በማምጣት ኢትዮጵያን ከአፍሪካ ተመራጭ መዳረሻ ሀገር እንድትሆን ለማድረግ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ተብሏል፡፡
ይህ ፖሊሲ በቅርቡ ወደሚመለከተው አካል ቀርቦ እንደሚፀድቅ የሚጠበቅ ሲሆን ተግባራዊ በሚሆንበት ወቅት ዘርፋን ተወዳዳሪ እንደሚያደርገው ይጠበቃል።
በቅድስት ደጀ
