ምያንማር የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በሀገሪቱ ከተከሰተው የመሬት መንቀጥቀጥ አደጋ መትረፋቸውን ዛሬ ለዶይቸ ቬለ ገለፁ። ወደ ሀገራቸው ለመመለስ እየተጠባበቁ ያሉት እነዚህ ኢትዮጵያውያን አሁንም ወታደራዊ የጦር ሰፈር ውስጥ ተጠልለው ያሉ ሲሆን ወደ ምያንማር የሄዱት በተለያዩ አጭበርባሪዎች ተታለው እንደሆነ ከዚህ በፊት ከዶይቸ ቬለ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ተናግረዋል። «እዚህ ያለው ማኅበረሰብ ኮሚቴ ስለሆንኩ ትክክለኛውን ቁጥር አውቀዋለው፤ 252 ነን።» ያለን ማይክ ፤ ኢትዮጵያውያኑ ያሉበት ቦታ በመሬት መንቀጥቀጡ ከፍተኛ አደጋ አለመከሰቱን ለዶይቸ ቬለ ተናግሯል።
«ውጪ ነበርን ፤ ለተወሰነ ጊዜ መሬት ተንቀጥቅጦ ነበር። አንድ ሕንጻ ላይ ትንሽ መሰንጠቅ ተከስቷል። ሌላ ጉዳት ግን አልደረሰም » ብሏል። እንዲያም ሆኖ ኪያው ካን የሚባል አካባቢ ታይላንድ ድንበር አቅራቢያ የሚገኙት ኢትዮጵያውያን ዳግም የመሬት መንቀጥቀጥ ቢከሰት የሚለው እያሰጋቸው እንደሆነ እና ወታደራዊ ጦር ሰፈር ውስጥ ሁለት ወር ሊሆናቸው እንደሆነ በጭንቀት ተናግረዋል። ስለሆነም « መንግሥት በአፋጣኝ ከዚህ ቦታ እንድንወጣ እንዲተባበረን እንጠይቃለን» ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።
ከአራት ቀናት በፊት በምያንማር የተከሰተውን ከባድ የመሬት መንቀጥቀጥ አስመልክቶ የዓለም ጤና ድርጅት (WHO) ከፍተኛ የሚለውን የአደጋ ጊዜ ደረጃ አውጇል። በሬክተር መለኪያ 7.7 የተመዘገበው የመሬት መንቀጥቀጥ በምያንማርን እና ጎረቤት ሀገር ታይላንድ ከፍተኛ ጉዳት ካደረሰ በኋላ የሕይወት አድን ሥራ እና ፍለጋው እንደቀጠለ ነው። በአደጋው እስካሁን ከ1,700 ሰዎች በላይ ሕይወታቸው አልፏል፤ ከ3,400 በላይ በሚሆኑት ላይ ደግሞ ጉዳት ደርሷል።
«ከመሬት መንቀጥቀጡ ተርፈናል፤ ግን ስጋት ላይ ነን» ምያንማር የሚገኙ ኢትዮጵያውያን
Date:
