አሜሪካ ከአለም ጤና ድርጅት አባልነቷ በይፋ መልቀቋን ካሳወቀች በኋላ፣ ካሊፎርኒያ የድርጅቱን የአለም አቀፍ የበሽታዎች መቀስቀስ ምላሽ ስርዓት ተቀላቅላለች።
ስርዓቱ ከ360 በላይ የቴክኒክ ተቋማትን በውስጡ ያቀፈ ሲሆን፣ በሽታዎች በተለያዩ ሃገራት ሲቀሰቀሱ ሃብትና ባለሙያዎችን በመላክ ምላሽ ሲሰጥ ለተግባሩ ማሳያ ደግሞ በኮቪድ 19 ወቅት የሰጠው ምላሽ ነው።
የካሊፎርኒያ ግዛት ገዢ ጋቪን ኒውሰም የአሜሪካ ከአለም ጤና ድርጅት የመውጣት ውሳኔ ተገቢ አይደለም ብለው በመተቸት ውሳኔው ብዙዎችን ይጎዳል ብለዋል።
ገዢው በዚህ ሳምንት በዳቮሱ ጉባኤ ከአለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ቴድሮስ አድሃኖም(ዶ/ር) ጋር መገናኘታቸው ሲገለጽ፣ በስርዓቱ እና በሌሎች የጤና ጉዳዮችም ካሊፎርኒያ ያላትን ትብብር እንደምትቀጥልም ገዢው ገልጸዋል።
ሮይተርስ
