ፖለቲከኞችና የማህበረሰብ አንቂዎችን ጨምሮ ጋዜጠኞች እንዲሁም ሌሎች በአማራ ክልል በተቀሰቀሰው በትጥቅ የታገዘ ግጭት ጋር በተያያዘ በእስር ላይ የሚገኙት ግለሰቦች ከእስር ሊፈቱ ነው መባሉን የእነ ክርስቲያን ጠበቃ ሰለሞን ገዛኸኝና ቤተሰቦቻቸው “ ምንም የደረሳቸው መረጃ እንደሌለ ” ተናግረዋል፡፡
እየተሰራጨ በሚገኘው መረጃ ይፈታሉ ከተባሉት መካከል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባሉ ክርስቲያን ታደለ የሚገኙበት ሲሆን ከመጪው ገና በዓል በፊት ከእስር እንደሚፈቱ እንደሚጠበቅም በማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች እየተሰራጩ የሚገኙት መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
በእርግጥ መንግስት ከዚህ ቀደም በ2014 የገና በዓል እንደ እስክንድር ነጋ፣ ጀዋር መሐመድ፣ ስብሃት ነጋን ያሉትን ጨምሮ ሌሎችንም ፖለቲከኞች በተመሳሳይ በበዓሉ ዕለት እንደለቀቃቸው ይታወሳል፡፡
ጠበቃ ሰለሞን ምንም አልደረሰንም ያሏቸው መረጃዎች ግን በመጀመሪያ ዙር ከእስር ይፈታሉ ተብሎ ከሚጠበቁት መካከል ዮሐንስ ቧያለው፣ ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻው፣ ክርስቲያን ታደለ፣ ሲሳይ አውግቼው፣ ቴዎድሮስ ኃይለማርያም፣ ወንድወሰን አሰፋ፣ መስከረም አበራ፣ ጫኔ ከበደ እና ካሳ ተሻገር እንደሚገኙበት ተመላክቷል፡፡
በሌላ በኩል የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በእነ ዮሐንስ ቧያለው መዝገብ በክርስቲያን ታደለ ላይ ከመጋረጃ ጀርባ የቀረበውን ምስክር ተከትሎ በዐቃቤ ህግ ባቀረበው ሰነድ ላይ አስተያየት ለመስጠት ለጥር 30 ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱን አዲስ ማለዳ ከዚህ ቀደም መዘገቧ አይዘነጋም፡፡
አዲስ ማለዳ
