በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ህግጋት መሰረት ከአጽዋማት መካከል አንዱ በሆነው ረቡዕ እና አርብ እለት የልደት በዓል ቢውል ይጾማል ? ወይስ ፍስክ ነው ? (የጥሉላት ምግብ ስጋ፣ ቅቤ ፣ ወተት፣ እንቁላል … ይበላል ?) የሚሉ ጥያቄዎች በሰፊው ቀርበዋል።
በቤተክርስቲያኗ ህግጋት መሰረት አንዱ የጾም ጊዜ በሆነው ረቡዕና አርብ እለት የልደት በዓል ቢውል ይጾማል ? ወይስ ይበላል ? ለምን ? ሲል የጠየቃቸው የቤተክርስቲያኗ ሊቃውንት፣ ፍስክ መሆኑን ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የመሪ እቅድ መመሪያ ኃላፊ መላከሰላም ሰለሞን ቶልቻ እንዳሉት፣ የልደት በዓል ረቡዕ፣ አርብ እለት ቢውል ” በፍትሐ ነገሥት በተደነገገው ” መሰረት አይጾምም።
ጥምቀት ረቡዕ ወይም አርብ ቢውል ማክሰኞ ወይም ሐሙስ ተጹሞ (ገሃድ/ጋድ ይባላል) የበዓሉ እለት (ረቡዕ ወይም አርብ) የፍስክ እንደሚበላ ገልጸው፣ ” በዓለ ልደት ግን ገሃድ/ጋድ የለውም። ምክንያቱም በጾም ላይ ጾም የለም ” ብለዋል።
” በፍተሐ ነገሥት አንቀጽ 15 ቁጥር 603 እንደተደነገገው የልደት በዓል ረቡዕ ወይም አርብ ቢውል የደስታ ቀን ስለሆነ አይጹሙት ይላል ” ሲሉም ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ገልጸዋል።
ለምን እንደማይጾም ምክንያታቸውን ሲያስቀምጡም፣ ” ምክንያቱም በጌታ መወለድ ሰው እና መላዕክት፣ ምድራዊያንና ሰማያውያን የታረቁበት፤ የጥሉ ግድግዳ የፈረሰበት እለት ስለሆነ ነው ” ብለዋል።
የልደት በዓል ረቡዕ ወይም አርብ ቀን ቢሆን የማይጾመው፣ ” በፍትሐ ነገሥት ስለተቀመጠ፤ በቀኖና መፅሐፍት ላይ የተደነገገ ስለሆነ ነው ” ሲሉም አስረድተዋል።
” በሞት ጥላ መካከል ላለ ህዝብ ነጻነት እንደተሰበከ ሁሉ የልደት በዓል የደስታ ቀን በዓል ነው። የአበው የተስፋ ቃል፤ የነብያት ትንቢት የተፈጸመበት፤ እግዚአብሔር ለአዳም የሰጠው ቃልም የሚፈጸምበት የደስታ ቀን ነው ” ብለዋል።
” ይህ ቀን የሀዘን ቀን አይደለም፤ የደስታ ቀን ስለሆነ አበው በፍትሃ ነገስት እንዳስቀመጡት በዓለ ልደትን ረቡዕ፣ አርብ እለት ቢውል እንደማይጾም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቀኖና እና ስርዓት የተደነገገ ነው ” ሲሉ ገልጸዋል።
” ዮም ፍሰሃ ኮነ በእንተ ልደቱ ነው ለእግዚእነ፤ (በጌታ መወለድ ደስታ ሆነ) እያልን የምንዘምርበት ነው ” የሚሉት መጋቢሰላም ሰለሞን፣ ” በዚህ ቀን የፍስክ ምግብ ነው የምንበላው፤ አይጾምም። ገሃድ/ጋድን በተመለከተ የጥምቀት በዓል ረቡዕ፣ አርብ ቢውል ማክሰኞ ወይም ሐሙስ ይጾማል። ገሃድ ማለት ለውጥ ስለሆነ ” ብለዋል።
” የልደት በዓል በጾመ ድህነት (ረቡዕ እና አርብ) ላይ ከዋለ አይጾምም ” ብለው፣ ” ስለዚህ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምዕመናን፣ በዓሉን በዋዜማው በቤተክርስቲያን አጥቢያ በመሄድ ምሽቱን በማህሌት፣ በስብከት፣ በጸሎት እንደሚተጉ፣ ከሌሊቱ 6 ሰዓት ላይ ቅዳሴ እንደሚገባ፤ ከዚያ ማክሰኞ ለረቡዕ አጥቢያ በመፈሰክ በዓሉ እንደሚከበር ገልጸዋል።
ተመሳሳይ ጥያቄ ያቀረብንላቸው፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጽ/ቤት የቅርሳ ቅርስ ቤተ መጽሐፍትና ወመዘክር መምሪያ ኃላፊ የሆኑት በኩረ ትጉሃን ቀሲስ ምትኩ ከንቲባ በበኩላቸው፣ “ይበላል” ሲሉ መልሰዋል።
@tikvahethiopia
