የቡድን 7 አገራት አሜሪካ እና እስራኤል ከቴህራን ጋር ጦርነት ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ የተከሰተውን ከፍተኛ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪን ለመቋቋም ከክምችታቸው እንዲለቀቅ እንደሚደግፉ አስታወቁ።
አገራቱ ከዓለም አቀፉ የኢነርጂ ኤጀንሲ (አይኢኤ) ጋር ተገናኝተው የተነጋገሩ ሲሆን፣ ከረቡዕ ከሰዓት ጀምሮ በነዳጅ ገበያ ውስጥ ትልቁ ነው የተባለውን መጠን ከመጠባበቂያ የነዳጅ ክምችታቸው መልቀቅ ይጀምራሉ።
የፋርስ ባሕረ ሰላጤ ግጭት በሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ በኩል የሚጓጓዘውን የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ ሙሉ በሙሉ ያስቆመና በቀጣናው የሚመረተው ነዳጅ ዘይት እንዲቀንስ ያደረገ ነው።
ግጭቱ ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ የተባለ ጭማሪ አሳይቷል።
ነገር ግን የነዳጅ ክምችት ከቡድን ሰባት አገራት ሊለቀቅ እንደሚችል ከተዘገበ በኋላ አንዳንድ ባለሙያዎች እርምጃው የአጭር ጊዜ መፍትሄ ብቻ እንደሚሆን ተናግረዋል።
ዓለም አቀፉ የኢነርጂ ኤጀንሲ ከ300 እስከ 400 ሚሊዮን በርሜል የነዳጅ ዘይት ሊለቅ ይችላል ተብሏል። ይህም ሩሲያ በ2022 መጀመሪያ ላይ ዩክሬንን ሙሉ በሙሉ ወረራ ባደረገችበት ወቅት ከተለቀቀው በእጥፍ ይበልጣል።
ይህ መጠን የሁለት ወይም የሦስት ቀን የዓለም አቀፍ ገበያ አቅርቦት አልያም ከሆርሙዝ ሰርጥ ለሁለት ሳምንት የሚጓጓዘውን የሚተካ ብቻ ነው።
የቡድን ሰባት የኢነርጂ ሚኒስትሮች ረቡዕ ዕለት ከአይኢኤ ጋር ባደረጉት ስብሰባ በኋላ “በመርህ ደረጃ፣ ስትራቴጂካዊ ክምችቶችን መጠቀምን ጨምሮ ሁኔታውን ለመፍታት ቅድመ ጥንቃቄ የተሞላባቸው እርምጃዎችን ተግባራዊ ማድረግን እንደግፋለን” ብለዋል።
ሁሉም የዓለም አቀፉ ኢነርጂ ኤጀንሲ አባል አገራት ዓለም አቀፍ መስተጓጎል ቢከሰት ለ90 ቀናት የሚበቃ መጠባበቂያ ነዳጅ መያዝ ይጠበቅባቸዋል።
