የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ እንደ ልህቀት ማዕከል፣ የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ደግሞ በሁለተኛ ዲግሪ የትምህርት መርሃ ግብር ካሪኩለም ቀርፀው የኒውክለር ቴክኖሎጂን ማስተማር መጀመራቸው ተገለጸ፡፡
በዘንድሮ የትምህርት ዘመን ከውጪ ሃገራት የኒውክለር ቴክኖሎጂ ትምህርት መስጠት የሚያስችላቸውን ስልጠና አግኝተው የተመለሱ መምህራን እንዳሉ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ጠቁሟል፡፡
በሚኒስቴሩ የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ክፍል ኃላፊና የኒውክለር ፕሮግራም አስተባባሪ ተክለማርያም ተሰማ፥ የኒውክለር ቴክኖሎጂ ትምህርት መስጠት የሚችሉ ዜጎችን በሩሲያና ቻይና ስልጠና አግኝተው እንዲመለሱ እየተደረገ ነው ሲሉ ለአራዳ ኤፍኤም ተናግረዋል፡፡
ሀገሪቱ ለዚህ ቴክኖሎጂ የሚያስፈልጋትን የሰው ኃይል ወደ ውጪ እየላከች ማሰልጠን አትቀጥልም ያሉት አስተባባሪው፤ እዚሁ የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ለኢትዮጵያ የኒውክለር ቴክኖሎጂ የወደብ ያህል ያስፈልጋታል ሲሉም በአፅንዖት መናገራቸው ተዘግቧል፡፡
