የአርሲ ዞን ጠቅላይ ዓቃቢ ህግ ጽ/ቤት
በ2017 ዓ.ም ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከሙስና ፣ ከሰነዶች ምዝገባ እና ከተለያዩ የወንጀል ድርጊቶች በአጠቃላይ 560 ሚሊዮን ብር ለመንግስት ገቢ ማድረጉ ተገልጿል ።
በሙስና 26 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ 5 ሄክታር መሬት ፣7 ሚሊዮን 9መቶ 4ሺህ 8መቶ ጥሬ ገንዘብ ፣ 18 ሚሊዮን 536 ሺህ 777 ብር የሚያወጣ 16 ዘመናዊ መኖሪያ ቤት ፣ አንድ የእርሻ ተሽከርካሪ ትራክተር ፣ ውሳኔ ተሰጥቶበት በአጠቃላይ ሰላሳ ስድስት ሚሊዮን ስድስት መቶ ሰባ ሺህ ብር ገቢ ሆኗል።
በሙስና ነክ የወንጀል ድርጊቶች 68 መዝገቦች ቀርበው በ74 ግለሰቦች ላይ ከስድስት ወር እስከ 10 ዓመት ውሳኔ መተላለፉን ብስራት ሬዲዮ ከፅህፈት ቤቱ ያገኘው መረጃ ያመላክታል። በኢኮኖሚ ነክ ወንጀሎች 118 መዝገቦች ተጣርተው 99 መዝገቦች ውሳኔ ሲያገኙ ከባንክ በብድር ተወስዶ ያልተመለሰ 56 ሚሊዮን ዘጠኝ መቶ ሰባ ሰባት ሺህ ብር ተመላሽ መደረጉ ተጠቁሟል ።
አንድ መቶ ስልሳ ሚሊዮን ሶስት መቶ ሰላሳ ሁለት ሺህ ብር በኦዲት ግኝት 22 ሚሊዮን አንድ መቶ ሰባ አንድ ሺህ ሰባት መቶ ስድስት ብር ደግሞ በሰነዶች ማስተካከያ ገቢ ተደርጓል። በሌላ በኩል የመንግስት ንብረት ለማስመለስ በተደረገ ክርክር አምስት የቀበሌ ቤቶች ፣ 24 ለሱቅ የተሰሩ የሸራ ቤቶች አርባ ሰባት ሺህ አራት መቶ ሰላሳ ሰባት ሄክታር የገጠር መሬት እና የደን ሀብት ማስመለስ ተችሏል። ያለአግባብ ተገዝተው በግለሰብ እጅ የገቡ 10 ላፕቶፕ ኮምፒውተር ተመላሽ ሆነዋል።
ከሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ 10 ሚሊዮን ሁሉት መቶ ሁለት ሺህ አምስት መቶ ሰማንያ ሶስት ብር ገቢ ተደርጓል ። በተለያዩ ከ30 በላይ በሚሆኑ የመንግስት እና መንግስታዊ ባልሆኑ መስሪያቤቶች ላይ በተደረገ ፍተሻ ከደንብ እና መመሪያ ውጪ የተሰሩ ስራዎች ተፈትሸው የማስተካከያ ስራዎች ተሰርተዋል።
በአጠቃላይ የአርሲ ዞን ዓቃቤ ህግ በዘጠኝ ወራት የስራ ክንውን ከ560 ሚሊዮን ብር ባላይ ለመንግሥት ገቢ እንዲደረግ ያደረገ ሲሆን 427 የተለያዩ የክስ መዝገቦች ተመስርተው 237 የሚሆኑት ተገቢ ውሳኔ የተሰጠባቸው መሆኑ ተገልጿል ። ከዚህ ሌላ 1436 የክስ መዝገቦች በፈጣን ችሎት ውሳኔ መሰጠቱን አርሲ ዞን ፖሊስ መምሪያ የተገኘው መረጃ ያመለካታል።
@ብስራት ሬዲዮ
በኤደን ሽመል
