የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ዶ/ር እመቤት መለሰና የባንኩ የአመራር አባላት፣ በሰበታ ከተማ የሚገኘውን የቢሜት የኢነርጂና ቴሌኮም ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማሕበርን ጎበኙ፡፡
የባንኩ ፕሬዚዳንት ዶ/ር እመቤት መለሰ ከጉብኝቱ በኋላ በሰጡት አስተያየት፤ ድርጅቱ ከፍተኛ አቅም የፈጠረና እንደ ሀገርም ለሚካሄደው የኢኮኖሚ ሽግግር ከፍተኛ አስተዋጽ የሚያደርግ ሥራ እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የጉብኝቱም ዓላማ ድርጅቱ ያለበትን አሁናዊ አቋም በመገምገም፣ በቀጣይ ከባንኩ ጋር ያለውን ግንኙነት ጤናማና ውጤታማ ማድረግ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ለመወያየት እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ታደሰ አድማሱ በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ ልማት ባንክ የገንዘብና ቴክኒክ ድጋፍ የተቋቋመው ቢሜት ኬብል ማምረቻ፣ በሀገራችን ከሚገኙ ኬብል አምራች ኩባንያዎች አንዱና ዋነኛው መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ሥራ አስፈጻሚው የቢሜት የኢነርጂና ቴሌኮም፣ ለትልልቅ ግንባታዎችና መሠረተ ልማት የኤሌክትሪክና ኮምዩኒኬሽንስ ኬብሎችን የሚያቀርብ መሆኑን ጠቅሰው፣ እንደሀገር በተጀመረው የማክሮ ኢኮኖሚ ግንባታ የበኩሉን ሚና እየተወጣ ነው ብለዋል፡፡
በቀጣይም ይህንን ሀገራዊ ፋይዳ ያለውን ድርጅት የበለጠ አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ለማስቻል ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ ጋር በሚኖረው ግንኙነት ላይ ውይይት ማድረግና በጋራ መሥራት እንደሚገባም ገልጸዋል፡፡
