በመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት የአየር ክልል መዘጋቱን ተከትሎ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ቀጠናው የሚደረጉ በረራዎችን ላልተወሰነ ጊዜ መሰረዙን ዛሬ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።
አየር መንገዱ በረራ ካቋረጠባቸው መዳረሻዎች መካከል ኦማን፣ ቤይሩት፣ ባህሬን፣ ቴል አቪቭ፣ ዶሃ፣ ኩዌት፣ ዱባይ፣ ሻርጃህ፣ አቡ ዳቢ እና ዳማም ይገኙበታል።
ኩባንያው ውሳኔውን ያስተላለፈው መንገደኞች ለተጨማሪ እንግልት እንዳይዳረጉና ደህንነታቸው የተጠበቀ እንዲሆን ለማስቻል መሆኑን ገልጿል።
በረራ በተሰረዘባቸው መስመሮች ላይ ትኬት ለቆረጡ መንገደኞችም አየር መንገዱ ሦስት አማራጮችን ያቀረበ ሲሆን እነሱም በረራዎች ዳግም ሲጀምሩ ያለምንም ተጨማሪ ክፍያ በሌላ ቀን መጓዝ፤ ጉዞን ወደ አቅራቢያ መዳረሻዎች ማዞር እና ጥቅም ላይ ላልዋለ ትኬት ሙሉ ክፍያን ተመላሽ ማድረግ ናቸው።
አየር መንገዱ የቀጠናውን ሁኔታ በቅርበት እየተከታተለ መሆኑን ጠቅሶ፣ ለተፈጠረው መስተጓጎል ለደንበኞቹ ይቅርታ ጠይቋል።
መንገደኞች ወደ አየር ማረፊያ ከመሄዳቸው በፊት የበረራቸውን ሁኔታ በአየር መንገዱ የዲጂታል አማራጮች እንዲያረጋግጡም ጥሪ አቅርቧል።
