የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ በመጪው ሰኞ አሜሪካን እንደሚጎበኙ የሃገሪቱ ባለስልጣናት አስታወቁ። የኔታንያሁ ጉብኝት አሜሪካ ከእስራኤል በምታስገባቸው ሸቀጦች ላይ የጫነችውን የ17 በመቶ ቀረጥን በተመለከተ ለመነጋገር ነው ተብሏል።
አንድ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የእስራኤል ባለስልጣን ለሮይተርስ የዜና ወኪል እንዳሉት ኔታንያሁ ከፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ጋር የሚያደርጉት ውይይት የተጣለውን ቀረጥ በማስነሳት ላይ ያተኮረ ነው።
ውይይታቸው የኢራን እና የሒዝቦላህ ጉዳይ ያካትት እንደሆን የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤት ማረጋገጫ መስጠት አልቻለም ነው የተባለው።
የአሜሪካው ፕረዚደንት ዶናልድ ትራምፕ በተለያዩ ሐገራት ላይ እየጣሉት ያለው የገቢ ዕቃዎች ቀረጥ አካል ነው የተባለለት አዲስ የቀረጥ ፖሊሲ መሰረት አሜሪካ ከእስራኤል በሚገቡ ዕቃዎች ላይ የ17 በመቶ ቀረጥ መጣሏን ታውቋል።
የእስራኤል የፋይናንስ ሚኒስቴር በበኩሉ ይህ አዲስ የተጣለው ቀረጥ እስራኤል ወደ አሜሪካ በምትልካቸው ማሽኖችና የሕክምና መገልገያ ዕቃዎች ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንደሚኖረው ገልጿል።
እስራኤልና አሜሪካ ከዛሬ 40 ዓመታት በፊት የገቢ ዕቃዎች ከቀረጽ ነጻ እንዲገቡ መስማማታቸውን ይታወቃል።
