
የእስራኤል መከላከያ ኃይል “በኢራን አገዛዝ” ላይ አካሄድኩ ያለውን “መጠነ ሰፊ ጥቃት” ማጠናቀቁን ሲያስታውቅ፤ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት አስቸኳይ ስብሰባ ሊያደርግ ነው።
እስራኤል ከአሜሪካ ጋር በመቀናጀት ቅዳሜ ጠዋት በኢራን ላይ በከፈተችው ጥቃት “አንዱ ዒላማ የነበረው በምዕራባዊ ኢራን ኬርማንሻህ አካባቢ ያለው ዘመናዊ የአየር ጥቃት መከላከያ ሥርዓት” እንደነበረ የእስአኤል ጦር ገልጿል።
ጦሩ በመግለጫው የተፈጸሙት ጥቃቶች “የኢራን አብዮታዊ ዘብ አቅምን ለማዳካም እና በእስራኤል ላይ ሊፈጸሙ የሚችሉ ጥቃቶችን ለማምከን የእስራኤል አየር ኃይል በኢራን አየር ክልል ውስጥ የሚያካሂደውን ጥቃት ያለ እንቅፋት ለመፈጸም የሚሰስችል ነው” ብሏል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የመንግሥታቱ ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ዛሬ ቅዳሜ በኒው ዮርክ የሰዓት አቆጣጠር ከሰዓት በኋላ በተፈጸመው ወታደራዊ ጥቃት ላይ ለመነጋገር አስቸኳይ ስብሰባ ጠርቷል።
ስብሰባው እንዲካሄድ የጠየቁት ባህሬን፣ ኮሎምቢያ፣ ቻይና፣ ሩሲያ እና ፈረንሳይ ሲሆኑ፣ የመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ቀደም ብለው “በመካከለኛው ምሥራቅ የታየውን ወታደራዊ ጥቃት” አውግዘዋል።
ዋና ፀሐፊው ባወጡት መግለጫ ወታደራዊ ጥቃቶቹ ዓለም አቀፍ ሰላምን እና ደኅንነትን የሚጎዱ በመሆናቸው “በአስቸኳይ እንዲቆሙ” ጠይቀዋል።
