ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ በዴንደን የእንግዳ ማረፊያ የኦማን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ባድር ቢን ሃማድ አል ቡሳይዲን ተቀብለው ማነጋገራቸው ዳጉ ጆርናል የሀገሪቱ የመረጃ ሚኒስተር አቶ የማነ ገብረመስቀል ካጋሩት መረጃ ተመልክቷል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከኦማኑ ሱልጣን ሃይታም ቢን ታሪቅ ለፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን ማሻሻያ እንዲሁም አህጉራዊ እና አለም አቀፋዊ የጋራ ተጠቃሚነትን በሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ የተላከ መልዕክት አስተላልፈዋል።
በኤርትራ እና ኦማን መካከል ያለው ታሪካዊ እና የቆየ ግንኙነት የሁለቱንም ሀገራት የጋራ ጥቅም ወደ ፊት ለማራመድ ምቹ መሆኑን ፕሬዝዳንት ኢሳያስ ተናግረዋልም ተብሏል። በአህጉራዊ እና አለም አቀፋዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ አመለካከቶችን እና ራዕይን በማጎልበት የሁለትዮሽ ግንኙነቶች የበለጠ ማጠናከር እንደሚቻልም ፕሬዝዳንት ኢሳያስ ተናግረዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ባድር ቢን ሃማድ ለኤርትራ ዜና አገልግሎት በሰጡት አጭር መግለጫም ከፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር በነበራቸው ቆይታ ለተደረጉት ውጤታማ የሃሳብ ልውውጥ አድናቆታቸውን ገልጸዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በኤርትራ እና ኦማን መካከል ያለውን አመለካከት ሙሉ በሙሉ በማጣጣም በሚመለከታቸው ቀጠናዊ ሀገራት መካከል ቀጣይነት ያለው ትብብር እና የጋራ መርሃ ግብሮችን እንዲሁም በአጠቃላይ የአከባቢውን ደህንነት እና መረጋጋት በተለይም የቀይ ባህር እና የአረብ ባህረ ሰላጤ ድህንነች ማረጋገጥ አለባቸው ማለታቸውን ዶጉ ጆርናል ተመልክቷል።
