የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች የሚያነሷቸውን ረጅም ጊዜ ተሰልፎ መቆየት፣ ብልሹ አሰራር፣ አሽከርካሪዎችን ገንዘብ መጠየቅ እና መሰል ጥያቄዎች ባሉበት ቦታ ሆነው ማቅረብ የሚችሉበት አሰራር መዘርጋቱ የትራንስፖርት እና ሎጀስቲክ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡
የሚኒስቴሩ የሕዝብ ግንኝነት ሥራ አስፈፃሚ አመለወርቅ እስቃኤል ለአሐዱ እንደተናገሩት፤ ሚኒስቴሩ በዘርፉ ላይ የሚስተዋለውን ችግር ለመፍታት በቴክኖሎጂ የተደገፈ አሰራር ዘርግቷል፡፡
ይህም በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራር መጀመሩ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ይገጥማቸው የነበረውን የመልካም አስተዳደር ችግር ይፈታል ተብሎ እንደሚጠበቅ አብራርተዋል።
የአሰራሩ ሂደቱ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ምዝገባ እና ፍቃድን ጨምሮ ከመረጃ ጋር በማቀናጀት ማስተዳደር እና አገልግሎት መስጠት የሚያስችል እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
አክለውም ብልሹ አሰራርን በመሰረታዊነት እንደሚፈታ አንስተው፤ አሽከርካሪዎች ባሉበት ባታ ሆነው ጥያቄ ማቅረብ እና ጉዳያቸውን ማስፈፀም እንደሚችሉ ገልጸዋል።
አሰራሩ ከሰው እጂ ንክኪ ነፃ መሆኑን የገለጹት ሥራ አስፈጻሚዋ፤ የተቀላጠፈ አሰራር እንዲኖር የትራንስፖርት እና ሎጀስቲክ ሚኒስቴር እየሰራ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ላይ የሚደርሰውን እንግልት እና በሕገ-ወጥ የፍተሻ ኬላዎች ያላግባብ ክፍያ መጠየቅና ማሰባሰብ ትልቅ ችግር መቀጠሉን የኢትዮጵያ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ማኅበር ለአሐዱ መግለጹ የሚታወስ ሲሆን፤ ይህንንም በከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ላይ እየደረሰ ያለውን የደህንነት ችግር ለመፍታት ከዋና ዋና የመንግሥት ተቋማት ጋር በመተባበር እየሰራሁ ነው ብሏል፡፡
