ዩኤስኤ አይ ዲ በትራምፕ አስተዳደር አስተዳደር ውሳኔ መሰረት አብዛኛውን ስራው እንዲቋረጥ መደረጉን ተከትሎ በስምንት ሀገራት የነበረው የኤች አይ ቪ መድኃኒት አቅርቦት አደጋ ላይ ጥሎታል የተባለ ሲሆን ነገሩ በአፋጣኝ እልባት ካላገኘ በሀገራቱ የመድኃኒቱ አቅርቦት ሙሉ በሙሉ ሊጠፋ ይችላል ሲል የዓለም ጤና ድርጅት አስጠንቅቋል።
ድርጅቱ እንደ ሄይቲ፣ ኬንያ፣ ሌሴቶ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ቡርኪና ፋሶ፣ ማሊ፣ ናይጄርያና ዩክሬን ያሉ ሀገራት በቀጣዮቹ ወራት በእጃቸው ላይ ያለውን የኤች አይ ቪ መድሓኒት እንደሚያልቅ ገልፆል። አክሎም ይህ መስተጓጎል ላለፉት 20 ዓመታት በኤች አይ ቪ ላይ የተሰራውን ስራ ወደ ኃላ የሚመልስ ነው ሲሉ የድርጅቱ ዳይሬክተር ጀነራል ዶክተር ቴድሮስ አድሓኖም ተደምጠዋል። ዳይኤክተሩ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት ማብራሪያ ይህ መስተጓጎል በዓለም አቀፍ ደረጃ አዳዲስ 10 ሚሊየን የቫይረሱ ተጠቂዎችና ወደ 3 ሚልየን የሚጠጉ በቫይረሱ ሳብያ የሚሞቱ ሰዎች ይኖራሉ ብለዋል።
ከዚህ ባሻገር የትራምፕ አስተዳደር ውሳኔ ኤች አይ ቪ፣ ፖሊዮ፣ ወባና ቲቪ የመሳሰሉ በሽታዎችን ለመከላከል የሚደረጉ ጥረቶች የሚያስተጓጉል ነው ተብሎለታል። የዓለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ጄነራሉ ዶ/ር ቴድሮስ አክለው አሜሪካ ቀጥተኛ የሆኑ ገንዘባዊ ድጋፎችን ለማቋረጥ ከወሰነች ሰብአዊና ስርዓት ባለው መንገድ ሀገራቱ ሌላ አማራጭ የመፍትሄ መንገድ የሚያገኙበት እድል የማመቻቸት ግዴታ አለባት ብለዋል።
ከዚህ በተጨማሪ የድጋፍ መቋረጡ በአፍጋኒስታን ከሚደረጉ የሰብአዊ ድጋፍና የጤና ነክ ስራዎች 80 በመቶዎቹ እንዲቋረጡ እንደሚያስገድድ የተገለፀ ሲሆን እእአ እስከ መጋቢት 4 ቀን ድረስ ባለው መረጃ መሰረት በዓለም አቀፍ ደረጃ 167 የጤና ተቋማት የተዘጉ ሲሆን አስቸኳይና አፋጣኝ የመፍትሄ እርምጃ ካልተወሰደም እስከ ሰኔ ድረስ ባለው ጊዜ ከ220 በላይ የጤና ተቋማት መዘጋታቸው አይቀሬ መሆኑ ተነግሯል።
