በተለያዩ ተቋማት ተጠንተው፤ ከድህነት ወለል፣ ከሕዝብ ቁጥር፣ ከዋጋ ግሽበት እና ከሌሎችም ጉዳዮች አንጻር ይፋ የሚደረጉ ሪፖርቶች የሚገለጹ ቁጥራዊ መረጃዎች፤ በጥንቃቄ መታየት እንደሚገባቸው የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት አሳስቧል፡፡
መቀመጫቸውን ሀገር ውስጥ ያደረጉትም ሆነ በሌሎች የዓለም ሀገራት የሚገኙት አጥኚዎች ቁጥራዊ መረጃዎችን ለተመለከተ ጥናታቸው፤ የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎትን ማማከር እንደሚገባቸው ያስታወሱት የተቋሙ ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሳፊ ገመዲ ናቸው፡፡
ኃላፊው አክለውም፤ ተቋሙ ኢትዮጵያን በተመለከተ ያሉ ሕጋዊ የቁጥር መረጃዎችን የሚሰጥ በመሆኑ ከእውቅናው ውጪ ያሉ መረጃዎች ተቀባይነት እንደማይኖራቸው ተናግረዋል፡፡
አንዳንድ ሀገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ተቋማት ከዋጋ ግሽበት፣ ከሕዝብ ብዛት፣ ከድህነት እና መሰል ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ይፋ የሚያደርጓቸው መረጃዎች የተጋነኑ እና የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ካለው መረጃ ጋር የተቃረነ የሚሆኑበት ጊዜ መኖሩንም ኃላፊው አቶ ሳፊ አንስተዋል፡፡
ለጥናት መነሻ የሚሆናቸውን መረጃ ከተቋሙ ያልተቀበሉና በራሳቸው መንገድ አጥንተው ቁጥራዊ መረጃዎችን ይፋ የሚያደርጉ ተቋማት የሚያሰራጩት መረጃ ትክክለኛ ያለመሆን ዕድል ስለሚኖረውም፤ ተገልጋዮች በመረጃው ከመገልገላቸው በፊት ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አሳስበዋል፡፡
ኃላፊው አያይዘውም ቁጥራዊ መረጃዎችን የመስጠት ኃላፊነት የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ ባለስልጣን መሆኑን የገለጹ ሲሆን፤ ጥናት ማድረግ የሚፈልጉ ተቋማትም ሆኑ ግለሰቦች የመነሻ መረጃውን ከተቋሙ መውሰድ እንደሚገባቸው እንዲሁም ያለ ባለስልጣኑ ፈቃድ ይፋ ማድረግ እንደማይችሉ ተናግረዋል፡፡
