የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የተጀመሩ የመንገድ ፕሮጀክቶች በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብ በቸልተኝነት ምክንያት እንዳይጠናቀቁ በሚያደርጉ ኮንትራክተሮች ላይ ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ አስጠንቅቋል።
የአስተዳደሩ የኮሙኒኬሽን ቡድን መሪ ዶክተር አስራት አሳሌ እንደተናገሩት፣ ሥራቸውን በአግባቡ በማያከናውኑ አካላት ላይ ኮንትራታቸውን ከማቋረጥ ባለፈ ሕጋዊ ሂደትን በመከተል ተጠያቂ የማድረግ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል።
በአሁኑ ወቅት በሀገር አቀፍ ደረጃ ወደ 170 የሚጠጉ የመንገድ ፕሮጀክቶች ግንባታ ላይ መሆናቸውን የገለጹት ዶክተር አስራት፣ ከእነዚህ መካከል ዘጠኝ የሚሆኑት መጠናቀቃቸውን አረጋግጠዋል።
ከተጠናቀቁት ፕሮጀክቶች መካከልም ሶዶ፣ ነገሌ ቦረና፣ ጅግጅና እና ድሬዳዋ፣ ጊቤ ወንዝ አካባቢ የተገነቡት ይገኙበታል። የቱሉ ቦሎ-ኬላ መንገድ ደግሞ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል ብለዋል።
ዶክተር አስራት በንግግራቸው የመንገድ ፕሮጀክቶች መጓተት ከኮንትራክተሮች አቅም ውስንነት በተጨማሪ፣ በአንዳንድ የሀገሪቱ ክልሎች ያለው የጸጥታ ሁኔታ እና ተያያዥ ጉዳዮች ግንባታው በተያዘለት ጊዜ እንዳያልቅ ምክንያት መሆናቸውን አብራርተዋል።
የመንገድ ሥራ ጥራትን በተመለከተ አስተዳደሩ የራሱ የሆነ የክትትል ክፍል እንዳለውና በየቦታው ተመድበው ሁኔታውን የሚከታተሉ መሐንዲሶች መኖራቸው ተገልጿል።
የአስተዳደሩ አመራሮችም በየወቅቱ በቦታው ድረስ በመውረድ የመስክ ምልከታ እንደሚያደርጉ የተገለጸ ሲሆን፣ ይህም የጥራት ደረጃውን ለመጠበቅና የግንባታ ፍጥነቱን ለማፋጠን የሚረዳ መሆኑ ተጠቁሟል።
