የትግራይ ክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር፣ የፌደራል መንግሥት በቅርቡ ለክልሉ በጀት ለመልቀቅ መስማማቱን ገለጸ፡፡
ውሳኔው በጊዜያዊ አስተዳደሩ ልዑክና በፌዴራል መንግሥት ባለስልጣናት መካከል ባሳለፍነው ሳምንት በአዲስ አበባ ከተካሄደው ውይይት በኋላ መተላለፉን የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዚዳንት ሌተናል ጄነራል ታደሰ ወረደ አስታውቀዋል፡፡
ውይይቱ የትግራይን የንግድ ማኀበረሰብ እየተፈታተኑ ያሉ ችግሮችን፤ በተለይም የባንክ ብድርና የወለድ ክፍያዎችን እንደዳሰሰ በመጠቆም፤ የተደረሱት ስምምነቶች ወደ ግጭት ላለመመለስ የሚደረገው ሰፊ ጥረት አካል እንደሆኑ ገልጸዋል።
“የፌዴራል መንግሥት የውስጥ ፖለቲካ ጉዳዮችን በውይይትና በመግባባት ለመፍታት ፈቃደኝነቱን አሳይቷል” ሲሉ ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል።
ጊዜያዊ አስተዳደሩ ውጥረቱን የበለጠ ሊያባብሱ በሚችሉ ድርጊቶች ውስጥ እንደማይሳተፍ ለፌዴራል ባለሥልጣናት ማረጋገጫ መስጠቱን ስፑትኒክ ዘግቧል፡፡
