ሞቲ ኢንጂነሪንግ ለኢትዮጵያ የልብ ሕሙማን ሕጻናት መርጃ ስምንት ሕጻናትን ለማሳከም የ2 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ማድረጉን በዛሬው ዕለት ተገልጿል። በየዓመቱ ታማሚ ሕጻናትን ለማከም ድርጅቱ ቃል ገብቷል።
በኢንፎርሜሽንና ቴክኖሎጂ (ICT)፣ በኔትወርክ መሰረተ ልማት፣ በኢ-ግብይት ሂደት፣ በድርጅት ሶፍትዌር ልማት፤ በዲጂታላይዜሽን፣ በሲስተም ኢንተግሬሽንና በATM አቅርቦት ዙሪያ አገልግሎት የሚሰጠው ኩባንያው፤ ለኢትዮጵያ የልብ ሕሙማን ሕጻናት መርጃ ድጋፍ አድርጓል።
በዚህ የድጋፍ ርክክብ ላይ የሁለቱም ተቋማት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች የተገኙ ሲሆን፣ ከዚህም በተጨማሪ በቀጣይነትም ድርጅቱ በየዓመቱ 4 ሕጻናትን ለማሳከምና ለማዕከሉ የአንድ ሚሊየን ብር ድጋፍ ለማድረግ መስማማቱ ተጠቁሟል።
ማዕከሉ በሚሰጣቸው የነጻ የልብ ቀዶ ሕክምና አገልግሎቶች የሕጻናትን ጤና በመመለስ በሕጻናት ዕድገትና ትምሕርት ላይ አዎንታዊ አስተዋጽዖ ማበርከት ሲችል፣ በዘርፉ የሰለጠኑ የጤና ባለሞያዎችን በማፍራትና ለልዩ ልዩ የትምሕርት ማዕከላት እንደ መማሪያ መዳረሻ እያገለገለ ይገኛል።
