የሱዳን ጦር ኃይል ከመዲናዋ ካርቱም ተነስቶ በተቀናቃኙ የፈጣን ደጋፊ ኃይሎች (አርኤስኤፍ) ከበባ ውስጥ ወደምትገኘው ኤል-ኦቤይድ ከተማ የሚወስደውን ዋና የትራንስፖርት መስመር ሙሉ በሙሉ መቆጣጠሩን ገለጸ።
በእሑድ ዕለት በሱዳን ጦር ኃይል ቁጥጥር ስር የገባው «አል ሳዳራት» የተሰኘው ዋና አውራ ጎዳና ኃይሉ፤ ወታደሮቹን፣ መሣሪያን፣ የነዳጅ እና የሎጂስቲክስ አቅርቦቶቹን በቀላሉ ለማንቀሳቀስ የሚረዳው ሲሆን፤ አርኤስኤፍ የሰሜን ኮርዶፋን ግዛት ዋና ከተማ የሆነችውን ኤል-ኦቤይድን ለመቆጣጠር የሚያደርገውን ግስጋሴ የሚያግድ ነው ተብሏል።
በከተማዋ ውስጥ ግማሽ ሚሊዮን ገደማ የሚሆኑ ዜጎች ተከበው የሚገኙ ሲሆን፣ ነዋሪዎቹ ለአርኤስኤፍ የድሮን ጥቃቶች በመጋለጣቸው አሰቃቂ የሰብአዊ ውጥረት ማንዣበቡን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ያስጠነቅቃል።
የሱዳን ጦር ባወጣው መግለጫ መሠረት፣ አውራ ጎዳናውን ተቆጣጥሮት ከነበረው የአርኤስኤፍ ኃይል ጋር ለሁለት ቀናት ያህል ከተካሄደው ከፍተኛ ውጊያ በኋላ፣ በካርቱም እና በኤል-ኦቤይድ መካከል የሚገኙ በርካታ ከተሞችንና መንደሮችን መልሶ መቆጣጠር ተችሏል።
