የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ የመራጮች ምዝገባ መጀመሩን ይፋ ባደረገ በመጀመሪያው ሳምንት ውስጥ፣ በመላ ሀገሪቱ በሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎች የተከሰቱ የቴክኒክና የሲስተም መቆራረጥ ችግሮች ሂደቱን እያስተጓጎሉት እንደሚገኝ ካፒታል ለመረዳት ችሏል።
ቦርዱ ምዝገባውን ዘመናዊ ለማድረግ “ምርጫዬ” የተሰኘ መተግበሪያንና በታብሌቶች የታገዘ የዲጂታል ምዝገባ ሥርዓትን ቢዘረጋም፣ በተግባር ግን ሲስተሙ መረጃዎችን በአግባቡ ባለመቀበሉ መራጮች ለከፍተኛ መጉላላት ተዳርገዋል። በተለይ በአዲስ አበባ፣ በደቡብ ኢትዮጵያ፣ በሲዳማ፣ በባህር ዳር እና በአዳማ አካባቢዎች ችግሩ በስፋት መስተዋሉን ተመላክቷል።
በምርጫ ጣቢያዎች የታዘቡትን የገለጹ መራጮች፣ “ሲስተም የለም” በሚል ሰበብ ለሰዓታት በፀሐይ ላይ እንደሚቆሙና ሳይመዘገቡ እንደሚመለሱ ተናግረዋል።
አስተያየታቸውን ለካፒታል የሰጡ መራጮች “ታብሌቱ እየሰራ አይደለም፤ ሰው በየቀኑ እየተንገላታ ነው። በተለይ አረጋውያን ሲመላለሱ ማየት ያሳዝናል” በማለት ቅሬታቸውን ገልጸዋል።
ከቴክኖሎጂው መቆራረጥ ጋር ተያይዞ፣ ዲጂታል አሰራሩ ውጤታማ ካልሆነ ቦርዱ ወደ ቀድሞው የወረቀት አሰራር እንዲመለስ የሚሉ ጥያቄዎች በስፋት እየቀረቡ ይገኛሉ።
የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወይዘሮ ሜላትወርቅ ኃይሉ፣ ምዝገባው በተጀመረ በመጀመሪያው ሳምንት 9.36 ሚሊዮን መራጮች መመዝገባቸውን ገልጸው፣ በሂደቱ ላይ ተግዳሮቶች መገጠማቸውን ግን አምነዋል።
ሰብሳቢዋ ለችግሩ መንስኤ ያሏቸውን ሁለት ዋና ነጥቦች የጠቀሱ ሲሆን፤ የመጀመሪያው የተመዝጋቢዎች ቁጥር እየጨመረ ሲመጣ የሲስተሙ የመሸከም አቅም ማነስ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ በአንዳንድ አካባቢዎች የኔትወርክ ሽፋን ደካማ መሆንና ከመብራት መቆራረጥ ጋር ተያይዞ የገጠሙ የኮኔክሽን ችግሮች መሆናቸውን አስረድተዋል።
ቦርዱ ችግሩን ለመፍታት ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በቅርበት እየሰራ መሆኑንና ለዚሁ ተግባር የሚከታተል ልዩ ግብረ ኃይል መቋቋሙን ገልጿል።
እስከ መጋቢት 28 ቀን 2018 ዓ.ም. በሚቆየው በዚህ የምዝገባ ሂደት፣ ያጋጠሙ የቴክኒክ ክፍተቶች በአፋጣኝ ታርመው ምዝገባው በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ እንደሚሰራ ቦርዱ አረጋግጧል።
