የትራምፕ አስተዳደር እነዚህ የአሜሪካ ቪዛ ያላቸው 55 ሚሊየን የውጪ ሃገር ዜጎች ከሃገር ሊያስባርራቸው የሚችል ጥፋት መስራታቸውን እየመረመረ ነው ተብሏል።
የአሜሪካ የውጪ ጉዳይ መስሪያ ቤት ሁሉም የአሜሪካ ቪዛ ያላቸው ሰዎች ተከታታይነት ያለው ምርመራ እንደሚደረግባቸውና ጥፋት ከተገኘባቸው ቪዛቸው እንደሚሰረዝ እና ከአሜሪካ እንደሚባረሩ ገልጿል።
የትራምፕ አስተዳደር ወደ ስልጣን ከመጣ በኋላ ህገወጥ ያላቸውን ስደተኞች ከአሜሪካ እያባረረ የቆየ ሲሆን በተለያዩ ሃገራት ዜጎች ላይም የቪዛ እገዳዎችን ሲጥል ቆይቷል።
የአሁኑ ውሳኔ ደግሞ ሁሉም የአሜሪካ ቪዛ ያለው የውጪ ዜጋ ላይ ምርመራ መጀመሩን ሲያሳይ በርከት ያሉ የአሜሪካ ቪዛ የያዙ ሰዎችንም ስጋት ውስጥ ከቷል።
የውጪ ጉዳይ መስሪያ ቤቱ ለአሸባሪ ድርጅቶች ድጋፍ ማድረግን ጨምሮ ከቪዛ ጊዜያቸው በላይ የቆዩና በወንጀል ተግባር የተሳተፉ ሰዎች እንደዚሁም ማህበራዊ ሚዲያን ጨምሮ በየትኛውም መንገድ የፀረ አሜሪካ እይታን ያንፀባረቁ ሰዎች በየተኛውም ጊዜ ቪዛቸው ሊሻር እንደሚችልና ከአሜሪካ ሊባረሩ እንደሚችሉ አስጠንቅቋል።
ባለፈው አመት በአሜሪካ 12.8 ሚሊየን ሰዎች የግሪን ካርድ የነበራቸው ሲሆን 3.6 ሚሊየን ሰዎች ደግሞ በጊዜያዊ ቪዛ በአሜሪካ ቆይተዋል።
Source: AP, The Guardian
