በአፋር ክልል የሚገኙ የትግራይ ታጣቂዎች የሚፈጽሙት ማንኛውም ትንኮሳ የፌደራል መንግስት ወይንም የአፋር ክልል መንግስት ትንኮሳ አደርገን ነው የምንወስደው ሲሉ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት ሌተናል ጀነራል ታደሰ ወረደ ገለጹ።
የክልሉ የሰማዕታት ኮሚሽን ባዘጋጀው መድረክ ላይ ትላንት ሐምሌ 8 ቀን 2017 ዓ.ም ተገኝተው ንግግር ያደረጉት ሌተናል ጀነራል ታደሰ ወረደ “በዚያ በኩል የሚኖር ምንም አይነት ተነሳሽነት/እንቅስቃሴ እንደ ትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር፣ እዚያ ያሉ ሀይሎች ብቻ አድርጎ አይወስደውም፣ ወይ የፌደራል መንግስት ነው ካልሆነም የአፋር መንግስት ነው ብሎ ነው የሚወስደው” ብለዋል።
“እዛ ካሉት (ነጻ መሬት) ሀይሎች ጋር ያለው ልዩነት መቶ በመቶ መፈታት ያለበት በሰላማዊ መንገድ ነው፤ ነገር ግን ማንኛውም ትንኮሳ ከአፋር ክልል በኩል ከመጣ ወይ የአፋር መንገስት ነው አልያም የፌደራል መንግስቱ ነው ተብሎ የሚወሰድ እንጂ የትግራይ ተወላጆች /ተጋሩ ተደርጎ የሚወሰድ አይደለም” ሲሉም አስታውቀዋል፤ታጣቂዎች “የውክልና (Proxy) ሀይሎች ሁነው እንዳያገለግሉ የሚቻለንን ሁሉ እናደርጋለን ሲሉ መደመጣቸውንም ነው አዲስ ስታንዳርድ በዘገባው ያመላከተው፡፡
